Wednesday, June 19, 2019

ኮሎኔል መንግሥቱን ትግል ለመግጠም ቤተመንግሥት የሄደው ደራሲ አውግቸው ተረፈ BBC Amharic

አውግቸው ተረፈ የብዕር ስሙ ነው። ወላጆቹ ያወጡለት ስም ኅሩይ ሚናስ ነው። የብዕር ስሙ ግን ይህ ብቻ እንዳልሆነ ደራሲ እንዳለ ጌታ ከበደ ለቢቢሲ ይናገራል።

በአጫጭር ልብወለድ፣ በትርጉም፣ እንዲሁም በአርታኢነት የሚታወቀው ኅሩይ ሚናስ ውልደቱ አዲስ አበባ አይደለም። ከጎጃም ደጀን ነው፤ ወደ አዲስ አበባ መጥቶ አይነ ስውራንን ይመራ ነበር።
ወደ አዲስ አበባ እንደመጣ ራሱን ለማኖር በረንዳ ላይ አድሯል። ቀስ በቀስ የፀሎት መጻህፍትን ወደ መሸጥ ከዚያም በሂደት የትምህርትና የልብ ወለድ መጻህፍትን ሸጧል።
መጻህፍት ንግድን ያስተማራቸው እነ አይናለም ዛሬ በጥሩ ሁኔታ የሚንቀሳቀሱ መጻህፍት ሻጮና አከፋፋይ ሆነዋል ይላል እንዳለ ጌታ ከበደ።
አውግቸው መጻህፍት ሻጭ በነበረበት ወቅት እርሱ እያነበበ ተመሰጦ ሳለ የመግዛት ፍላጎት ያለው ሰው ሲመጣ ውሰደው ብሎ በነጻ እንደሚሰጥ ይነገርለታል።
ለደራሲ አበረ አዳሙ ከአውግቸው ስራዎች "ወይ አዲስ አበባ"ን የሚያክል የለም። "ወይ አዲስ አበባ" የአውግቸው የራሱ ታሪክ ነው ይላሉ።
ለአቶ አበረ አውግቸው ጭምት ደራሲ ነው። በዚህ ሀሳብ የ"አለመኖር" ደራሲው ዶ/ር ዳዊት ወንድማገኝም ይስማማሉ።
ሁለቱም ደራሲያን ብዙ ማውራት አይወድም። በጥልቀት ያስባል ሲሉ አቶ አበረ አክለው የመርህ ሰው ነው ብለዋል።
አቶ አበረ ለአውግቸው የመርህ ሰውነት የሚጠቅሱት በ19 87ና 88 ዓ.ም አካባቢ የሆነውን በማስታወስ ነው "በዚህ ዓመት የማነበው መዝገበ ቃላት ነው ካለ አመቱን ሙሉ ቃሉን ጠብቆ የሚያነበው ያንኑ ነው።"
አቶ አበረ "እንደው ለመሆኑ አውግቸው ጓድ መንግሥቱን ትግል እገጥማለሁ ብሎ ቤተ መንግሥት መሄዱን ታውቃላችሁ?" አሉን።
"አረ በጭራሽ" የኛ መልስ ነበር። አውግቸው አንድ ዕለት ወደ ብሔራዊ ቤተ መንግሥት ሄዶ ኮሎኔል መንግሥቱን ጥሩት አለ። "ለምን?" ሲሉት "ትግል እገጥመዋለሁ መልሱ ነበር።
"ይህንን ... "ብሎም እላፊ ተናገረ።
እኔን ትግል ገጥሞ መጣል ሳይችል አገር መግዛት ይችላል መከራከሪያው ነበር።
ወታደሮቹ አፈፍ አድርገው ደበደቡት። ከዚያም እስር ቤት ወርውረውት ለበርካታ ጊዜ ታስሮ ነው የወጣው ይላሉ አቶ አበረ።
"ይህ መቼ ነው የሆነው አልናቸው?" ሰባዎቹ መጀመሪያ ይመስለኛል አሉ በመጠራጠር።
"ኅሩይ ርትዑነት ያረበበበት ቀና ሰው ነበር የሚለው" እንዳለጌታ አሮጌ መጻህፍትን እየሸጠ የጻፋቸው አጫጭር ልብ ወለዶች የካቲት መጽሔት ላይ ታትመው መነበብ መጀመራቸውን ይናገራል። ለዚህ ደግሞ ምክንያት የሆነው መፅሐፍት ከእርሱ እየገዛ ያነብ የነበረው ስብሀት ገብረ እግዚያብሄር እንደሆነ እንዳለ ጌታ ያስታውሳል።
ያኔ አሮጌ መጻህፍት እየሸጠ ሲጽፍ ጓደኞቹ አንተን ብሎ ደራሲ ብለው እንዳይዘባበቱበት ስለፈራ በብዕር ስም ነው ትረካው መጽሔት ላይ እንዲወጣ ያደረገው።
አውግቸው ብዙ የብዕር ስሞች አሉት የሚለው እንዳለጌታ፣ ራሱ ነገረኝ በማለት አዳነ ቸኮል የእርሱ የብዕር ስም መሆኑን አጫውቶናል።
በዚህ የብዕር ስም፣ በአዳነ ቸኮል 'የአማልክትና የጀግኖች አፈ ታሪክ' የሚል ሥራ ታትሞ ለንባብ በቅቷል፤ አዳነ ቸኮል የአያቱ ስም ነው።
የአውግቸውን በርካታ ሥራዎች ከተመለከተና ካነበበ በኋላ "የአደፍርስ ደራሲ ዳኛቸው ወርቁ አውግቸውን ኩራዝ አሳታሚ ወስዶ በአርታኢነት አስቀጥሮታል" የሚለው እንዳለጌታ ኩራዝ አሳታሚ በርካታ ሥራዎችን ሰርቷል ሲል ምስክርነቱን ይሰጣል።

ከአሮጌ መጽሐፍ ሻጭ ወደ ደራሲነት

ተዋናይት፣ ጸሐፌ ተውኔት፣ የጥበብ ተቆርቋሪ ዓለምፀሐይ ወዳጆ

“ጥበብ ለእኔ እንደ ሱስ ነው፤ ከጥበብ ተለይቼ መኖር አልችልም”
                        ዓለምፀሐይ ወዳጆ

             ሕይወቴን በሙሉ ያሳለፍኩት በኪነ ጥበብ ውስጥ በተዋናይነትና  በገጣሚነት ሙያ ነው:: ወደ አሜሪካ ከመጣሁ በኋላ ኑሮን ለማሸነፍና ቤተሰቤን ለማስተዳደር ያልሰራሁት ሥራ የለም፡፡ እንዲያም ሆኖ ግን ከምወደው ሙያ አልተለየሁም፡፡ ጥበብ ለእኔ እንደ ሱስ ነው፤ ከጥበብ ተለይቼ መኖር አልችልም፡፡ በዚህ ዓለም ላይ ዳግም የመኖር ዕድል ቢሰጠኝ፣ የምመርጠው የአሁኑን ሙያዬን፣ መሆን የምፈልገውም የአሁኗን ዓለምፀሐይን ነው፡፡ 
እኔ በተወለድኩ ጊዜ፣ እናቴ 16 ዓመቷ ነበር፡፡ ወዲያው አባቴ በግሪክ አገር ሥነ መለኮት የመማር ዕድል አግኝቶ ስለሄደ ያደግሁት፣ ፍቅር በተሞላበት የአያቶቼ ቤት፣ የጠየቅሁት ሁሉ እየተሟላልኝ ነበር:: የልጅነት አርአያዬ የሆነችው ማራኪዋና ከሰው ተግባቢዋ ሴት አያቴ፤ ተግቶ መስራትንና ለጋስነትን አስተምራኛለች፡፡ ሁሌም “መኖር ብቻውን ትርጉም የለውም፤ ሌሎችንም መርዳት አለብሽ” ትለኝ ነበር፡፡ ጥበብን እንደ ነፍሷ ነበር የምትወደው፡፡ ታንጎራጉራለች፡፡ በአሮጌ ቴፕዋም ሙዚቃ ታዳምጥ ነበር፡፡ ለመጀመርያ ጊዜ ወደ ሀገር ፍቅር ቴአትር ቤት ወስዳ ተውኔት ያሳየችኝ እሷ ናት፡፡ የግጥምና የድራማ ፍቅር የተጋባብኝም ከእርሷ ነው ማለት እችላለሁ፡፡ 

አስተማሪዎቼ ለኪነ ጥበብ ያለኝን ፍላጎትና ተሰጥኦ የተረዱት ገና ታዳጊ ሳለሁ ነበር፡፡ በ13 ዓመቴ እኔን ለሌሎች ምሳሌ በማድረግ የአማርኛ አስተማሪዬ፣ ግጥሜን ለተማሪዎች ድምጹን ከፍ አድርጎ አንብቦልኛል፡፡ በዚያው ዓመት በየክፍለ ሀገሩ እየዞረ ለሚያሳየው ቲያትር፣ ተማሪዎችን ይመለምል የነበረው የሙዚቃ አስተማሪዬ መላኩ አሻግሬ፤ በሀገር ፍቅር ቴያትር መድረክ ላይ እንድተውን ዕድል ሰጠኝ፡፡ እዚያው ቲያትር ቤት በነበረ የአማተር ክበብ ውስጥም አባል ሆንኩኝ፡፡ ይህ የቲያትር ፍላጎቴ ግን ቤተሰቤ ውስጥ አከራካሪ ጉዳይ ነበር፡፡ አባቴ ከግሪክ እንደተመለሰ በትምህርቴ አንደኛ እንድወጣ ብቻ ሳይሆን ሐኪም ወይም ጠበቃ መሆን እንዳለብኝ ቁርጤን ነገረኝ፡፡ መድረክ ላይ ቢያየኝ እግሬን መስበር ብቻ ሳይሆን እንደሚገድለኝም ጭምር አስጠነቀቀኝ:: አያቴ ግን እንድተውን ፈቀደችልኝ፡፡ በእርግጥ እሷም ብትሆን ቅድመ ሁኔታ አስቀምጣልኝ ነበር:: ትምህርቴን ማጠናቀቅ እንዳለብኝና ምስሌ በፖስተር ወይም በበራሪ ወረቀት ላይ እንደማይወጣ ቃል አስገባችኝ፡፡ ትያትር የምሰራው ሕዝብ ፊት እንደመሆኑ ትወናዬን ከአባቴ መደበቁ አስቸጋሪ ነበር:: ሁልጊዜ መድረክ ላይ ስተውን ድንገት አባቴ ከተፍ ቢልብኝ በማለት፣ ሁሌም ተክቶኝ የሚሰራ ተዋናይ አዘጋጅ ነበር፡፡ 

Tuesday, June 11, 2019

‹ችግራችሁ ይህ ነው የሚለውን የምዕራባውያን አተያይ መሞገት መቻል አለብን››

ኤልሳቤጥ ወልደ ጊዮርጊስ (ዶ/ር)፣ የኢትዮጵያ ጥናት ተቋም የቀድሞ ዋና ዳይሬክተር
ኤልሳቤጥ ወልደ ጊዮርጊስ (ዶ/ር) ለስድስት ዓመታት ያህል የኢትዮጵያ የጥናት ተቋምን በዋና ዳይሬክተርነት መርተዋል፡፡ በመቀጠልም በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አለፈለገ ሰላም ትምህርት ቤትና የአፍሪካና ኦሪዬንታል ጥናት ማዕከል መምህር በመሆን በማገልገል ላይ ናቸው፡፡ በቅርቡ ‹‹Modernist Art In Ethiopia›› በሚል ርዕስ ጥናታዊ መጽሐፋቸው በኦሀዮ ዩኒቨርሲቲ ፕሬስ አማካይነት ታትሞላቸዋል፡፡ መጽሐፉ በመጪው ወር በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አማካይነት ይመረቃል ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን፣ በውጭ አገር የሚኖሩ በርካታ ኢትጵያውያንም እያነበቡት ነው፡፡ ባሳተሙት አዲስ መጽሐፍ ውስጥ ያሉ ዘመናዊነት፣ የዘመናዊነት ዓለም አቀፋዊና አገራዊ የታሪክ ሒደቶች፣ እንዲሁም ጽንሰ ሐሳቡ ለኢትዮጵያ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ዕድገት ያበረከተው አስተዋጽኦና የጎደለውን ነገር አስመልክቶ ነአምን አሸናፊ አነጋግሯቸዋል፡፡
ሪፖርተር፡- አዲስ ባሳተሙት መጽሐፍ ውስጥ የተለያዩ የታሪክ ሒደቶችን ከዘመናዊነት አንፃር የተደረጉ ተሞክሮዎችን ለመዳሰስ ሞክረዋል፡፡ ነገር ግን የታሪክ ሒደቶቹን ከመመልከታችን በፊት፣ ዘመናዊነት የሚለው ጽንሰ ሐሳብ በኢትዮጵያውያን ልሂቃን ዘንድ የተለያየ አረዳድና ትርጓሜ ስለሚሰጠው ከብያኔው ለመነሳት ያህል ዘመናዊነት ምንድነው?
ኤልሳቤጥ ወልደ ጊዮርጊስ (ዶ/ር)
ዶ/ር ኤልሳቤጥ፡- ዋናው እንግዲህ የመጽሐፌ ንድፈ ሐሳብ ይህ ዘመናዊነት የምንለው ነገር እንዴት እንደምንረዳው ነው፡፡ ዘመናዊነት ማለት ዘምኖና ዘንጦ መሄድ፣ የመሳሰሉትን ነገሮች ለመግለጽ የተለመደ አመለካከት አለ፡፡ ዘመናዊ አለባበስ፣ ዘመናዊ አመጋገብ፣ ወዘተ፡፡ ከእሱ በላይ ግን በመጽሐፌ ዘመናዊ ርዕዮተ ዓለም ወይም ጽንሰ ሐሳብ ላይ ነው መነጋገር የፈለግኩት፡፡ እናም ዘመናዊነት የሚለው ጽንሰ ሐሳብ እኛ አገር ውስጥ እንዴት ሰረፀ? እንዴትስ ሄድንበት? ያ ጽንሰ ሐሳብ የት አደረሰን? መከራ ላይ ጣለን? አብላላነው፣ ተነጋገርንበት፣ ወዘተ የሚሉትን መሠረታዊ የዘመናዊነት ምልከታዎችን ነው ላነሳ የፈለኩት፡፡ ወደ አገር ቤት ከመጣበሁት ጊዜ ጀምሮ የታዘብኩት ነገር፣ ይህ የዘመናዊነት ጽንሰ ሐሳብ በቅጡ ያልተብላላ፣ ብዙ ክርክር የሚያስፈልገው፣ የብሔር ግጭትና የዘመናዊ ትምህርት አካሄድን ጨምሮ እዚህ ደረጃ ያደረሰን ይህ የዘመናዊነት ጽንሰ ሐሳብ ላይ በደንብ መነጋገር አለመቻላችን ነው፡፡ ምሁራኖቻችንም በቅጡ አይወያዩበትም፡፡ እናም ችግር እየሆነ መጥቷል፡፡ ወደድንም ጠላንም ዘመናዊነትን ማሰብ የምንችለው አሁን ያለንበትን አውሮፓዊ ዕይታ ውስጥ ሆነን በተፈጠረው ባህላዊና ኢኮኖሚያዊ ትስስር ማዕቀፍ ውስጥ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ጫና ያለበት ቢሆንም፣ ተዋረዳዊ ስለሆነ ሁሉ ነገራችንን አስተሳስሮናል፡፡ ባህሉን፣ አመለካከቱንና ትምህርት አሰጣጡንም፡፡ ስለዚህ ይህ ከምን ጋር ነው የመጣው? ዘመናዊነት ከሚለው ከአውሮፓዊ ጽንሰ ሐሳብ ጋር ነው የመጣው፡፡
 በመጽሐፌ መግቢያ ላይ እንደምገልጸው ደግሞ ይህ ጽንሰ ሐሳብ በቅኝ ግዛት መንገድ ነው የመጣው፡፡ በአንድ በኩል ከኢንዱስትሪ አብዮት በኋላ፣ በሌላ በኩል የአብርሆት ዘመን ሰዎች አመዛዛኝ ምክንያታዊ ነፃነት ሊኖራቸው ይገባል፣ በራሳቸው ነገሮችን እንዲወስኑና እንዲሠሩ ይገባል ከሚለው ተራማጅ አስተሳሰብ ጋር በተያያዘ የመጣ ነው ማለት ነው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ የዘመናዊነት ታሪክ የአመፅ ታሪክ ነው፡፡ አመፁ ምንድነው አፍሪካ ሄዶ ቅኝ ይገዛ ነበር፡፡ ከበርሊን የመቀራመት ስምምነት ጀምሮ ይህ ምዕራባዊ ኃይል አፍሪካን ብቻ ሳይሆን፣ እስያንና ደቡብ አሜሪካን በጭካኔ የገዛበት ሒደት ነው፡፡ ሁለተኛው ባርነት በሰፊው የተካሄደበት፣ አፍሪካውያን አዲስ ዓለም ወደሚባለው በጭካኔ ተሸጠው የሄዱበት ጊዜ ነው፡፡ ስለዚህ ይህ የዘመናዊነት ታሪክ ሁለት ገጽታ ይኖረዋል፡፡ አንደኛው ጭካኔ በተሞላበት አኳኃን በቅኝ ግዛት መንገድ የሚገለጽ ሲሆን፣ ሌላኛው ደግሞ የአውሮፓውያን የአብርሆት ዘመን የመጣበት፣ በተለይ ከፈረንሣይ አብዮት በኋላ የመጣው አመለካከት ነው፡፡ እንግዲህ የአመፃውንና የቅኝ ግዛቱን ታሪክ ስንመለከት ለምንድነው ያስፈለገው ሲባል፣ በርካሽ የሠራተኛ ጉልበት አውሮፓን ለማበልፀግ የተደረገ ነው፡፡ አውሮፓን ለማበልፀግ ደግሞ ሀብት የተወሰደበት ነው፡፡ የአውሮፓን ኢኮኖሚ ለማዳበር እነዚህ ሁሉ ጭካኔዎች ተከናውነዋል፡፡    

ሪፖርተር፡- ዘመናዊነት ትርጓሜው በዚያ መንገድ ከሆነ ኢትዮጵያ ደግሞ ቅኝ አልተገዛችምና ይህ ትርክት እንዴት ነው ኢትዮጵያ ላይ የሚሠራው?
ዶ/ር ኤልሳቤጥ፡- ትልቁ ችግራችን ይህ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ነፃ ሆና ኖራ ታውቃለች ወይ? እንግዲህ የዝመና ዘመን ብዬ የምለው ከዓድዋ ድል በኋላ ነው፡፡ ከዓድዋ በኋላ ያልኩበት ምክንያት ዘመናዊነት የታሪክ ሒደት ስላለው ነው፡፡ የዘመን ሒደቱም ከኢንዱስትሪ አብዮት ጀምሮ ከዚያ ሄደ የሚል አለ፡፡ ያ የዘመን ሒደት ግን በእኛ ዓይነት በቅኝ በተገዙ አገሮች ላይ አይሠራም፡፡ ምክንያቱም ሌላ ታሪክ ነው ያለው፡፡ በቅኝ ግዛት ታሪክ የአመፅ ታሪክ ስለሚመጣ የዘመን ሒደቱን የምንለካው በራሳችን ታሪክ ውስጥ ነው፡፡ ይህ የዘመን ሒደት ብያኔ በምዕራባውያንና በሌሎች ምሁራን መሀል ያለው ልዩነት፣ እነዚህኞቹን ከቅኝ ግዛት ነፃነት በኋላ ሲጀምሩ የእኛዎቹ ደግሞ ከየት እንደሚጀምሩ አይታወቅም፡፡ ኢትዮጵያ የሦስት ሺሕ ዓመት ታሪክ አላት ከሚለው ተነስተው ከዚያ ሊወስዱት ይችላሉ፡፡ ዘመናዊነት ልውጠት (Transformation) እስከሆነ ድረስ ላሊበላም፣ አክሱምም ሊሆን ይችላል፡፡ ነገር ግን የዘመናዊ ቅኝ ግዛታዊና የቅርብ ጊዜ ታሪክን ነው ማወቅ ያለብን፡፡ ያ ታሪክ ደግሞ ከ18ኛው ክፍለ ዘመን እስካሁን ያለውን ነው፡፡ ስለዚህ እኔ ዓድዋ ያልኩት ከዓድዋ በኋላ ብዙ ፈረንጆች ይመጣሉ፣ የዘመናዊ አገር ግንባታ ፕሮጀክት ተጀምሯል ብዬ አምናለሁ፡፡ በዚህ ጊዜ ባንኩ፣ ፖስታው፣ ጋዜጣው አለ፡፡ አንድ ወጥ የሆነ አገር ለመመሥረት ምኒልክ ወደ ደቡብ ያደረጉት ዘመቻ አለ፣ ወዘተ፡፡ ይህ ሁሉ የሚያሳየው የዘመናዊ አገር ግንባታን አንድ ምልከታ የምንወስድበት ነው፡፡
     ሁለተኛው ደግሞ የፈረንጆቹ መምጣት የግለሰቡን ወይም የማኅበረሰቡን የመዘመን ፍላጎትና አመለካከቶች የሚመጡበት ስለሆነ ነው፡፡ ከዚህ አንፃር ኢትዮጵያ ከዓድዋ ድል በኋላ ከአውሮፓዊ ጫና ወጥታ አታውቅም፡፡ ስለዚህ የቀጥታ ቅኝ ግዛት አይኑር እንጂ፣ በእጅ አዙር ከአውሮፓዊው ጫና ጋር የኖርን ሰዎች ነን፡፡ ስለዚህ ከሰፊው የዘመናዊነት ታሪክ ራሳችንን ልናወጣ አንችልም ብዬ እገምታለሁ፡፡ ነገር ግን ታሪካችን የተለየ ነው፡፡ ዘመናዊነትን በጊዜ ሒደት እንዴት ነው የምንገልጸው? ምክንያቱም ቅኝ ስላልተገዛን፡፡ የአገሪቱ የዘመናዊነትን ጽንሰ ሐሳብ አወሳሰድ ይህ ሁሉ ታሪክ አለው፣ ታሪኩ የተለየ ነው፡፡ ነገር ግን ከትልቁ የኢኮኖሚ ጫና ታሪክ ተላቀን አናውቅም፡፡ ስለዚህ የዘመናዊነት ታሪክ እኛንም እዚያ ውስጥ ይከተናል የሚለው የእኔ አመለካከት ነው፡፡ ነገር ግን ይህ ነገር አልተብላላም፡፡ እኔ ከዚያኛው ከቅኝ ግዛቱ ታሪክ ጋር አንቀላቀል እያልኩ አይደለም፡፡ ታሪካችን ልዩ ነው፡፡ ታሪካችንን የምናይበት መንገድ ግን ከዘመናዊው የቅኝ ግዛት ታሪክ ነፃ አይወጣም የሚል ነው፡፡  

Tuesday, July 3, 2018

“ዶ/ር ዐቢይ፤ የርዕዮተ ዓለምና የቀኖና እስረኛ አይደለም” Written by አለማየሁ አንበሴ

Dr .Dagnachew Asefa 


ዩኒቨርሲቲ የመወያያ መዲና እንጂ ከመንገድ የመጣን ሃሳብ ሁሉ መቀበያ አይደለም

    ከሦስት ዓመት በፊት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህርነታቸው የተባረሩትና ሰሞኑን በራሳቸው ጥያቄ፣ ወደ ማስተማር ሥራቸው የተመለሱት የፍልስፍና ምሁሩ ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ፤ እንዴት ወደ ዩኒቨርሲቲ እንደተመለሱ፣በሃገሪቱ እየታየ ስላለው የፖለቲካ ለውጥና ተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ ጋር ተከታዩን ቃለ ምልልስ አድርገዋል፡፡

    አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ማስተማር የጀመሩት እንዴት ነው?
ለብዙ ዓመታት አሜሪካን ሃገር ነው የኖርኩት፡፡ በቆይታዬ ብዙ ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ ስለመመለስ ነበር የማስበው፡፡ ወደ ሃገሬ ተመልሼ ማስተማር ነበር የምፈልገው፡፡ ለኔ ማስተማር የህይወት ጥሪ ነው፤ ሌላ ነገር መስራት አልችልም፡፡ እዚያም ሃገር የምሠራው አስተማሪነት ነበር፡፡ በዚህ መነሻ ወደ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፍልስፍና ትምህርት ክፍል አቅንቼ፣ “እናንተ ጋር ማስተማር እፈልጋለሁ፤”አልኩኝ፡፡ በወቅቱ ያነጋገርኳቸው ሓላፊም”ታዲያ አንተ ከፕ/ር አንድርያስ ጋር ትግባባለህ፣ ለምን ከሳቸው ጋር አትነጋገርም?” አሉኝ፡፡ “አይ እንደሱ አልፈልግም፤ በመተዋወቅ ሳይሆን በህጋዊ መስመር መጥቼ ነው መግባት የምፈልገው” አልኩ፡፡ በኋላም የዲፓርትመንቱ ሃላፊ ጋ ማመልከቻዬን አቅርቤ ተቀበሉኝ፤ በዚህ ሁኔታ ነው አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲን የተቀላቀልኩት፡፡ መግባቴን ፕ/ር አንድርያስ የሰማው በኋላ ነው፡፡  
ዩኒቨርሲቲ እያስተማሩ፣ በተለያዩ የፖለቲካ መድረኮች ላይ ሃሳብዎን ያቀርቡ ነበር…?
አሜሪካን ሃገር ለ10 ዓመታት ያህል አስተምሬያለሁ። በዚህ ቆይታዬ፣ ለሰው ልጅ፣ ነፃነት ሁለተኛው ተፈጥሮው መሆኑን አውቄያለሁ፡፡ አካዳሚክ ነፃነት ማለት ምን እንደሆነ ጠንቅቄ አውቃለሁ፡፡ ለምሳሌ፡- በ1919 በሁለት ፕሮፌሰሮች ተረቅቆ፣ አሁን ድረስ እውቅና ያለው የአካዳሚክ ነፃነት ምሶሶዎች (መርሖዎች) አሉ፡፡ አንደኛው፤ በትምህርት ክፍል ውስጥ በመረጠው ርእሰ ጉዳይ ለማስተማር የመቻል ገደብ የለሽ ነፃነት ነው፡፡ ሁለተኛው፤ በምርምር ያካበተውን እይታና ሐሳብ በመጽሐፍ የማሳተም ነፃነት ነው፡፡ ሦስተኛው፤ ዩኒቨርሲቲውን በሚመለከት ከአስተዳደርና አትክልተኛ እስከ ፕሬዚዳንቱ ጽ/ቤት ድረስ የመማር ማስተማር አሠራሩን የመተቸት መብት ነው፡፡ አራተኛው ምሶሶ፤ ስለ ሃገርህ ሁኔታ እንደ አንድ ዜጋ የፈለግኸውን ነገር የመናገር መብት ነው፡፡ እነዚህ ናቸው የአካዳሚያዊ ነፃነት ምሶሶዎች፡፡ ይሄን ይዤ አስተምራለሁ፤ በዚያው ልክ የምሁራዊ መብቴን ተጠቅሜ እተቻለሁ፡፡ 
እኔ በየመድረኩ ስናገር፣ እተች የነበረው፣ ይህን ተፈጥሮአዊ መብቴን ተጠቅሜ ነው፡፡ ልክ ኮንትራቴን አቋርጠው፣ “አታስተምር” ሲሉኝ፤ “አሁን ገና ኢትዮጵያዊ ሆንኩ” ነው ያልኳቸው፡፡ ምን ማለት ነው ተብዬ በብዙኃን መገናኛ ተጠየቅሁ፡፡ በወቅቱ የመለስኩላቸው፤”ኢትዮጵያዊ ማለት መብቱ የተረገጠ ነው፤የኔ መብት እስክባረር አልተረገጠም ነበር፤ አሁን ተረግጧል፤ ስለዚህ ኢትዮጵያዊ መሆኔን አረጋግጫለሁ፤” በማለት ነው፡፡ በርግጥም የሆነው እንደዚያ ነው፡፡ 
በዩኒቨርሲቲ ቆይታዎ ምንድነው  የታዘቡት?