Tuesday, July 3, 2018

“ዶ/ር ዐቢይ፤ የርዕዮተ ዓለምና የቀኖና እስረኛ አይደለም” Written by አለማየሁ አንበሴ

Dr .Dagnachew Asefa 


ዩኒቨርሲቲ የመወያያ መዲና እንጂ ከመንገድ የመጣን ሃሳብ ሁሉ መቀበያ አይደለም

    ከሦስት ዓመት በፊት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህርነታቸው የተባረሩትና ሰሞኑን በራሳቸው ጥያቄ፣ ወደ ማስተማር ሥራቸው የተመለሱት የፍልስፍና ምሁሩ ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ፤ እንዴት ወደ ዩኒቨርሲቲ እንደተመለሱ፣በሃገሪቱ እየታየ ስላለው የፖለቲካ ለውጥና ተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ ጋር ተከታዩን ቃለ ምልልስ አድርገዋል፡፡

    አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ማስተማር የጀመሩት እንዴት ነው?
ለብዙ ዓመታት አሜሪካን ሃገር ነው የኖርኩት፡፡ በቆይታዬ ብዙ ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ ስለመመለስ ነበር የማስበው፡፡ ወደ ሃገሬ ተመልሼ ማስተማር ነበር የምፈልገው፡፡ ለኔ ማስተማር የህይወት ጥሪ ነው፤ ሌላ ነገር መስራት አልችልም፡፡ እዚያም ሃገር የምሠራው አስተማሪነት ነበር፡፡ በዚህ መነሻ ወደ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፍልስፍና ትምህርት ክፍል አቅንቼ፣ “እናንተ ጋር ማስተማር እፈልጋለሁ፤”አልኩኝ፡፡ በወቅቱ ያነጋገርኳቸው ሓላፊም”ታዲያ አንተ ከፕ/ር አንድርያስ ጋር ትግባባለህ፣ ለምን ከሳቸው ጋር አትነጋገርም?” አሉኝ፡፡ “አይ እንደሱ አልፈልግም፤ በመተዋወቅ ሳይሆን በህጋዊ መስመር መጥቼ ነው መግባት የምፈልገው” አልኩ፡፡ በኋላም የዲፓርትመንቱ ሃላፊ ጋ ማመልከቻዬን አቅርቤ ተቀበሉኝ፤ በዚህ ሁኔታ ነው አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲን የተቀላቀልኩት፡፡ መግባቴን ፕ/ር አንድርያስ የሰማው በኋላ ነው፡፡  
ዩኒቨርሲቲ እያስተማሩ፣ በተለያዩ የፖለቲካ መድረኮች ላይ ሃሳብዎን ያቀርቡ ነበር…?
አሜሪካን ሃገር ለ10 ዓመታት ያህል አስተምሬያለሁ። በዚህ ቆይታዬ፣ ለሰው ልጅ፣ ነፃነት ሁለተኛው ተፈጥሮው መሆኑን አውቄያለሁ፡፡ አካዳሚክ ነፃነት ማለት ምን እንደሆነ ጠንቅቄ አውቃለሁ፡፡ ለምሳሌ፡- በ1919 በሁለት ፕሮፌሰሮች ተረቅቆ፣ አሁን ድረስ እውቅና ያለው የአካዳሚክ ነፃነት ምሶሶዎች (መርሖዎች) አሉ፡፡ አንደኛው፤ በትምህርት ክፍል ውስጥ በመረጠው ርእሰ ጉዳይ ለማስተማር የመቻል ገደብ የለሽ ነፃነት ነው፡፡ ሁለተኛው፤ በምርምር ያካበተውን እይታና ሐሳብ በመጽሐፍ የማሳተም ነፃነት ነው፡፡ ሦስተኛው፤ ዩኒቨርሲቲውን በሚመለከት ከአስተዳደርና አትክልተኛ እስከ ፕሬዚዳንቱ ጽ/ቤት ድረስ የመማር ማስተማር አሠራሩን የመተቸት መብት ነው፡፡ አራተኛው ምሶሶ፤ ስለ ሃገርህ ሁኔታ እንደ አንድ ዜጋ የፈለግኸውን ነገር የመናገር መብት ነው፡፡ እነዚህ ናቸው የአካዳሚያዊ ነፃነት ምሶሶዎች፡፡ ይሄን ይዤ አስተምራለሁ፤ በዚያው ልክ የምሁራዊ መብቴን ተጠቅሜ እተቻለሁ፡፡ 
እኔ በየመድረኩ ስናገር፣ እተች የነበረው፣ ይህን ተፈጥሮአዊ መብቴን ተጠቅሜ ነው፡፡ ልክ ኮንትራቴን አቋርጠው፣ “አታስተምር” ሲሉኝ፤ “አሁን ገና ኢትዮጵያዊ ሆንኩ” ነው ያልኳቸው፡፡ ምን ማለት ነው ተብዬ በብዙኃን መገናኛ ተጠየቅሁ፡፡ በወቅቱ የመለስኩላቸው፤”ኢትዮጵያዊ ማለት መብቱ የተረገጠ ነው፤የኔ መብት እስክባረር አልተረገጠም ነበር፤ አሁን ተረግጧል፤ ስለዚህ ኢትዮጵያዊ መሆኔን አረጋግጫለሁ፤” በማለት ነው፡፡ በርግጥም የሆነው እንደዚያ ነው፡፡ 
በዩኒቨርሲቲ ቆይታዎ ምንድነው  የታዘቡት?