መጻህፍት



ብርሃኑ ዘሪሁን እና “ድል ከሞት በኋላ”

 ባዩልኝ አያሌው



የአንዳንድ ፀሐፍቶቻችንን ብርታትና ትጋት፣ በዚህም ያበረከቱልንን ረብ ያላቸው ፍሬዎቻቸውን ሳስብ በመደነቅ ውስጤ ይሞላል፡፡ ሆኖም ብዙም ሳይቆይ እነዚህ ጠቢባንና ስራዎቻቸው እውቅና እና ትኩረት ማጣታቸውን ሳስብ ልቤ በቁጭት ይጨመቃል፡፡ እናም “እድል እና ቲፎዞ አቦ ላትመለሱ እንጦሮንጦስ ውረዱ!” ብዬ እራገማለሁ። የፀሐፊ ክፍያው መነበብ በመሆኑ አለመነበብ መከፋትን ቢጭርም ቅሉ የምር ፀሐፊ ይህንንም ቸል ብሎ መጻፉን ይቀጥላልና ስሜቱ የወል አይሆን ይሆናል፡፡ የምር እውቅና መስጠትስ መረዳትን የግድ ይል የለ። እንደዛ!
ብዙ ተግተው ብዙ ቢሰጡንም፣ ብዙም “ካልዘመርንላቸው” ብርቱ ደራሲዎቻችን አንዱ ብርሃኑ ዘሪሁን ይመስለኛል፡፡ ስለደራሲውና ስራዎቹ በጋዜጣ አምድ ላይ ለማውሳት መሞከር “ሆድ ላይሞሉ አጉል ማላስ” ቢሆንም፣ ካለማለት ጥቂት ማለት ያተርፋልና በዚህ ጽሑፌ ስለደራሲ ብርሃኑ ዘሪሁንና አስተዋጽኦዎቹ፣ እንዲሁም “ድል ከሞት በኋላ” ስለተባለው ድርሰቱ ጥቂት አወሳለሁ፡፡ 
በኢትዮጵያ ስነጽሑፍ ታሪክ ውስጥ ጉልህ ቦታ ሊሰጣቸው የሚገቡ ስራዎችን ካበረከቱ ደራሲያን አንዱ ብርሃኑ ዘሪሁን ነው፡፡ የአጭርና የረዥም ልቦለድ ደራሲ፣ ጸሐፌ ተውኔት እና ጋዜጠኛ የነበረው ብርሃኑ ከ1952 ጀምሮ ከዚህ ዓለም በሞት እስካለፈበት 1979 ዓ.ም ድረስ 11 ልቦለድ ድርሰቶችንና 3 የሙሉ ጊዜ ተውኔቶችን ለተደራሲያኑ እንካችሁ ያለ ብርቱ ብዕረኛ ነው፡፡ 
በ1952 ዓ.ም “የእንባ ደብዳቤዎች” የተባለ ድርሰቱን እንካችሁ በማለት ጉዞውን አንድ ያለው ብርሃኑ፤ በኋላም “ድል ከሞት በኋላ”፣ “አማኑኤል ደርሶ መልስ”፣ “የበደል ፍጻሜ”፣ “ጨረቃ ስትወጣ” እና “ብር አምባር ሰበረልዎ” የተባሉትን ድርሰቶቹን አበርክቶአል፡፡ እንዲሁም “የቴዎድሮስ እንባ” እና “የታንጉት ምስጢር” የተባሉ ሁለት ታሪካዊ ልቦለዶችንና በወሎ ክፍለ ሀገር ተከስቶ የነበረውን ድርቅና የመንግስቱን ቢሮክራሲ ህያው አድርጎ የከተበባቸውን “ማዕበል የአብዮት ዋዜማ”፣ “ማዕበል የአብዮት መባቻ” እና “ማዕበል የአብዮት ማግስት” የተባሉ 3 ልቦለዶችን አስነብቦአል፡፡ ይህ ብቻ አይደለም፤ “ጣጠኛው ተዋናይ”ን እና “አባ ነፍሶ”ን የመሰሉ ተውኔቶችንም ጽፎ ለመድረክ አብቅቶአል፡፡ 
የብርሃኑን ድርሰቶች በጥሞና ለመረመረ አንባቢ አንድ ነገር አይሸሸገውም፡፡ ይኸውም ደራሲው ከጊዜ ጊዜ እያደገና እየበሰለ መሄዱ ነው፡፡ ደራሲው በገፀ ባህርያት አሳሳል፣ በግጭት አፈጣጠር እና በአተራረክ ጥበብ እንዲሁም በአጻጻፍ ብልሀቱ እየሰላ ሲሄድ በድርሰቶቹ በጉልህ ይስተዋላል፡፡ ምንም እንኳን ሲመሰከር ባይሰማም ብርሃኑ አጭር፣ ቀጥተኛና ግልጽ አረፍተ ነገሮችን በድርሰቶች ውስጥ በመጠቀም፣ እንዲሁም ቀድሞ የነበረውን ተረታዊ የታሪክ መንገሪያ ስልት በመቀየር ፈር ቀዳጅ ከሆኑ የሀገራችን ደራሲያን አንዱ ነው፡፡ ድርሰቶቹን የሚጽፈው እጅግ ቀላል እና ግልጽ በሆነ ስልት ነው፡፡ ከይዘት አንጻር አብዛኞቹ ድርሰቶቹም የሚያተኩሩት ማህበራዊና ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ነው፡፡ 
የብርሃኑ ድርሰቶች ከቅርጽም ሆነ ከይዘት አንጻር ብዙ ሊባልላቸው የሚችሉ ናቸው፡፡ ሁሉም ድርሰቶቹ ማለት ይቻላል እጅጉን ለመነበብ የማይጎረብጡ ናቸው፡፡ ታሪክ ሲተርክም ሆነ መዋቅር ሲያበጅ ያውቅበታል፡፡ በየድርሰቶቹ የምናገኛቸው ገጸ ባህሪያቱ የቅርብ ሰዋችን ያህል የሚሰሙን ናቸው፡፡ የዚህም ምክንያቱ ምናልባት ማንነታቸው ከእኛ እንደ አንዱ ስለሆነ ታሪካቸውም እኛው የምንኖረው ያልራቀን፣ ያልረቀቀን አይነት ስለሆነ ይሆናል፡፡ በመሆኑም ስሜታቸውን ሁሉ እንድንጋራ እንሆናለን፡፡ የብዙዎቹ ድርሰቶቹ ጭብጦችም እንዲሁ ኑሮአችንና የየእለት ጉዳያችን ናቸው፡፡ 
ብርሃኑንና ድርሰቶቹን ሳስብ ሁሌም የሚደንቀኝ አንድ እውነት አለ፡፡ ያለኝ መረጃ እርግጥ ከሆነ ብርሃኑ ለብዙ ዓመታት ጋዜጠኛ፣ በኋላም የአዲስ ዘመን ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ነበር፡፡ የጋዜጣ ስራ ደግሞ ምን ያህል ጊዜን እንደሚወስድ ብቻ ሳይሆን አድካሚና የአፍታ ረፍት የለሽ መታተር እንደሆነ እናውቃለን። ዛሬ ለነገ ሰርቶ ዛሬውኑ ለቀጣዩ ቀን ማሰብን፣ መሮጥን ያለ ረፍት መድከምን… ይጠይቃል፡፡ ጋዜጣው እለታዊ ሲሆን ደግሞ አስቡት፡፡ የጋዜጣው አዘጋጅ ሲኮንስ? ሌላ ሌላውን ትተን ዋና አዘጋጁ ቢያንስ በየእለቱ ርዕሰ አንቀጽ መጻፍ ይጠበቅበታል። እንግዲህ በዚህ ሁሉ ውጥረት ውስጥ ሆኖ ነው ብርሃኑ በቁጥር የበዙ በጥራትም የላቁ ድርሰቶችን የጻፈው፡፡ ይህ ሁሌም ያስገርማኛል፡፡ 
“ድል ከሞት በኋላ” ብርሃኑ ዘሪሁን “የእንባ ደብዳቤዎች”ን ካቀረበ ከ3 ዓመታት በኋላ በ1955 ዓ.ም ያሳተመው ሁለተኛው ልቦለዱ ነው፡፡ ብርሃኑ ልቦለዱን የጻፈው በወቅቱ በደቡብ አፍሪካ ይካሄድ በነበረው የጥቁር ሕዝቦች የነጻነት ትግል ላይ ተመስርቶ ነው፡፡ የድርሰቱ ጭብጥ የነጻነት ትግል፣ ትኩረቶቹም በወቅቱ ነጻ ያልወጣችው ደቡብ አፍሪካ እና በነጮች ስር ሆነው በመሰቃየት ላይ የሚገኙት ህዝቦቿ ናቸው፡፡ የታሪኩ ስፍራ ደቡብ አፍሪካ፣ የልቦለዱ ገጸ ባህሪያትም ለነጻነት የሚታገሉት ጥቁር ደቡብ አፍሪካውያን እና ገዢዋቻቸው የሆኑት ነጮች ናቸው፡፡ 
ልቦለዱ የሚተርከው የደቡብ አፍሪካ ጥቁር ህዝቦች በነጮች ስለሚደርስባቸው ጭቆና እና ይህንን ጭቆና ለማስወገድ ጥቁሮቹ ስለሚያደርጉት ትግል ነው፡፡ በዘመኑ በደቡብ አፍሪካ የነበረው ጨቋኝ የነጮች አገዛዝ፣ የጥቁሮቹ በገዛ ሀገራቸው በባርነት መገዛት በዚህም ይደርስባቸው የነበረው ግፍና መከራ ሁሉ በልቦለዱ ግሩም በሆነ መልኩ ቀርቦአል፡፡ 
የልቦለዱ ዋና ገጸ ባህሪ የዙሉ ጎሳ አባል የሆነው ድኩማ ነው፡፡ የድኩማ አባት ኪሙይ በሚሰራበት የነጮች ንብረት በሆነው የዱቄት ፋብሪካ ውስጥ ከሌሎች የስራ ባልደረቦቹ ጋር ባነሱት የህክምና አበል ጥያቄ ምክንያት በነጮች ላይ ትልቅ ሤራ ጠንስሰዋል በሚል በሀሰት ተወንጅሎ ይታሰራል። አባቱ በመታሰሩ ምክንያት የቤተሰቡ ኃላፊነት ሙሉ በሙሉ በድኩማ ትከሻ ላይ ይወድቃል፡፡ ዘሩ ነጭ ቢሆንም የነጮቹን የግፍ አገዛዝ የሚቃወመውና ለጥቁሮቹ የሚቆረቆረው ዶክተር እስቴዋርድ ድኩማን የቆዳ ፋብሪካ ውስጥ በጉልበት ሰራተኛነት ያስቀጥረዋል፡፡
 ድኩማ በፋብሪካው እየሰራ ቤተሰቡን ለማስተዳደር ጥረት ቢያደርግም አባቱ በወንጀለኛነት ስለተፈረደበት ብቻ የወንጀለኛ ልጅ ነህ በሚል ምክንያት ከቆዳ ፋብሪካው ይባረራል፡፡ በድኩማ ቤተሰብ ላይም ከፍተኛ ችግር ይወድቃል። በዚህም ድኩማ የመከራው ጥልቀት እያንገሸገሸው ይመጣል።
ቆይቶም ሲያግዘው የቆየው እስቴዋርድ ዱርባን በምትባልና ጥቁሮች በሚኖሩባት ከተማ ለሚኖር አባ አሊንጎ ለተባለ ወዳጁ ድኩማን ላይ የደረሰበትን ችግር ሁሉ ገልጾ ደብዳቤ በመጻፍ እንዲረዳው ድኩማን ይልከዋል፡፡ ሆኖም አሊንጎ ስራ ሊያገኝለት ባለመቻሉ ድኩማ አሊንጎ ቤት መኖር ይጀምራል፡፡ በአሊንጎ መኖሪያ ቤት ማታ ማታ በየአካባቢው የሚኖሩ የጥቁሮች ተወካዮች ስለተጫነባቸው የመከራ ሕይወትና እንዴት ነጻ መውጣት እንደሚችሉ ያደርጉት የነበረው ውይይት ድኩማን እየሳበው ይመጣል፡፡ በሂደትም የውይይቱ አካል ይሆናል፡፡ 
ምክክሩና እቅዱ ቀጥሎ እነ አሊንጎ አመጹን ለማንሳት ምቹ ጊዜን እየጠበቁ ባሉበት ወቅት ድኩማ በፖሊስ ተይዞ ይታሰራል፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ለጥቁሮች ወደ ተከለከለው ኮከብ አደባባይ ገብቶ መገኘቱ ነበር። የድኩማ መታሰርም አመጹ ተጠንቶ እና ምቹ ሁኔታ ሲገኝ ያለ ደም መፋሰስ ነው መደረግ ያለበት የሚል አቋም የነበረውን አሊንጎን ተስፋ ያስቆርጠዋል። ስለዚህም አመጹ መካሄድ እንዳለበት ይወስናል፡፡ በመሆኑም ድኩማ ፍርድ ቤት በሚቀርብበት ሰዓት 50 ሺ ጥቁር ደቡብ አፍሪካውያን በሰልፍ ሆነው የተቃውሞ መዝሙር በመዘመር ወደ ፍርድ ቤቱ ያመራሉ። ሆኖም የነጭ ፖሊሶች ጥይት በመተኮስ የአመጹን መሪዎች ጨምሮ ብዙ ጥቁሮችን ይገድላሉ፡፡  ከፍርድ ቤቱ በመውጣት አመጹን የተቀላቀለው ድኩማ እና የትግሉ መሪ የነበረው አሊንጎም ከፖሊሶቹ በተተኮሰ ጥይት ይገደላሉ፡፡ የጀመሩት ትግል እንደሚቀጥል ተስፋ አድርገው፣ ሞታቸውን በጸጋ እንደተቀበሉት ተገልጾ ታሪኩ ይቋጫል፡፡
ታሪኩ እጅግ አጓጊና የማይሰለች፣ አተራረኩም ውብ ነው፡፡ እነ ድኩማና አባቱ ኪሙይ፣ አሊንጎ፣ ዶክተር እስቴዋርድ የመሳሰሉት የታሪኩ ባለቤቶች በውብ መንገድ የተቀረጹና ቅርባችን ያሉ ያክል የሚሰሙን አይረሴ ገጸ ባህሪያት ናቸው፡፡ 
ብርሃኑ ዘሪሁን ብዙዎቹን ታሪካዊ ልቦለዶቹን የጻፈው ታሪኩ የተፈጸመበት ቦታ በአካል ተገኝቶ መረጃዎችን በመሰብሰብና የሁነቱን መንፈስ ለመላበስ በመሞከር ነው፡፡ “የቴዎድሮስ እንባ”ን ሲጽፍ ጎንደርና መቅደላ፣ 3ቱን “ማዕበሎች” ሲጽፍ ደግሞ ከወሎ የገጠር ቀበሌዎች ደሴ እስከነበረው የስደተኞች ካምፕ ድረስ ተዘዋውሮ በድርቅ የተጠቁትን ሰዎች በማየትና በማነጋገር መረጃዎችን ሰብስቦአል፡፡ “ድል ከሞት በኋላ”ን ለመጻፍ ግን ደቡብ አፍሪካ አልሄደም፡፡ ያም ሆኖ ባለመሄዱ ከመቼትም ሆነ ከታሪክ አንጻር ምንም እንዳላጎደለና  የወቅቱን የደቡብ አፍሪካን ጥቁሮች የመከራ ህይወትና የነጻነት ትግል በጥሩ አቀራረብ ለአንባቢያን ማሳየቱን ብዙዎች ይስማሙበታል፡፡ 
ልቦለዱን ከራሱ ከደራሲው ስራዎችም ሆነ ከሌሎች በዘመኑና ከእሱም ቀድመው ከታተሙ ልቦለድ ድርሰቶች የሚለየው አንድ ጉዳይ አለ፡፡ ይኸውም የሌሎች ሕዝቦችን ታሪክ መተረኩ ነው፡፡ 
ቀደም ሲል ለድርሰቶቻቸው በእውኑ ዓለም የሌሉ መቼቶችን እየፈጠሩና ሰው ያልሆኑ ገጸ ባህሪያትን እየቀረጹ ጭምር የጻፉ ደራሲያን ቢኖሩም የሌላ ሀገርን ታሪክና መቼት በሙሉ ጊዜ በድርሰቱ ውስጥ በመገልገል፣ በአጠቃላይ የሌሎች ሕዝቦችን ጉዳይ የድርሰቱ አቢይ ትኩረት አድርጎ የጻፈ ደራሲ አላጋጠመኝም፡፡ ይህንን ለማንሳት የወደድኩት ደራሲው ይህንን ልቦለድ መጻፍን ለምን ፈለገ? ወደሚለው ጥያቄ ስለሚመራኝ ነው፡፡  
ደራሲው ስለመጽሐፉ የመጻፍ ምክንያት በከተበበት መግቢያ ላይ “መጽሐፉን የጻፍኩት ስለ ነጻነትና ስለመብት ለተሰዉ ሰዎች እና ወደፊትም በመታገል ላይ ለሚገኙት ሕዝቦች ሁሉ መታሰቢያ የምትሆን አንዲት ድርሰት ማበርከት እዳዬ ሆኖ ስለተሰማኝ ነው” ይላል፡፡ ሆኖም መጽሐፉ የታተመበትን ጊዜ (1955 ዓ.ም) እና በልቦለዱ የተነሱ ጉዳዮችን ይዘን ስናስብ አማራጭ የለንም ብለን እጅ ካልሰጠን በቀር ብርሃኑ ድርሰቱን ለመጻፍ ምክንያቴ ነው ያለንን ለማመን እንቸገራለን፡፡ ወቅቱ ምንም እንኳን የብዙ የአፍሪካ ሀገሮች የነበሩበትን መንፈስ ያህል ባይሆንም በኢትዮጵያም የለውጥ ነፋስ መንፈስ የጀመረበት ጊዜ ነው፡፡ እርግጡን መናገር ቢቸግርም ደራሲው ልቦለዱን ሲጽፍ ሌላ ዓላማ ያለው ይመስላል፡፡ ምናልባትም የደቡብ አፍሪካውን የነጻነት ትግል መንፈስ በዚህች ሀገር ወጣቶች ላይ ማጋባት፣ እኛም የተጫነን ቀንበር አለና ከተቀመጥንበት እንነቃነቅ የማለት… የመሳሰሉት አይነት ዓላማዎች፡፡ 
አስገራሚው ጉዳይ ታዲያ ይህንን የመሰለ የነጻነት ትግልን ጭብጡ ያደረገ ይህንንም በበርካታ  ሁነቶች ማሳየት የቻለ ልቦለድ፣ የለውጥ ነፋስ እየመጣባት ባለች ሀገርና ነፋሱን እየጠሩት ባሉት የዘመኑ ወጣቶች ሳይቀር ብዙም አለመነበቡ ነው፡፡ በወቅቱ ልቦለዱ 2,000 ኮፒ እንደታተመና ብዙም እንዳልተሸጠ፣ ለዚህም ምክንያቱ የዘመኑ አንባቢያን ለደቡብ አፍሪካ ታሪክ ብዙም ፍላጎት ያልነበራቸው በመሆኑ እንደሆነ ደራሲው (ብርሃኑ) ገልጾልኛል፤ በማለት የብርሃኑን የህይወት ታሪክ እና ስራዎቹን ያጠናው ሪዱልፍ ኬ. ሞልቬር Black Lions- The Creative Lives of Moderen Ethiopia’s Literary Giants and Pioneers (1997) በተባለው መጽሐፉ አስፍሮአል፡፡ መተላለፍ ይሉታል ይሄ ነው። 
Source; http://www.addisadmassnews.com/

‹‹Tower in the Sky›› እና ‹‹ይወስዳል መንገድ ያመጣል መንገድ›› 

  አንተነህ ተስፋዬ ለማ


 አዳም ረታ እና ሕይወት ተፈራ መንገዳቸው (ታሪካቸው) ገጥሞ (ተገጣጥሞ) አየዋለሁ፡፡ አንዱ ላንዱ ምስክር የቆሙ ይመስል . . . . በዘመን ባሕር ላይ የቁዘማ ታንኳቸውን ወደኋላ ይቀዝፋሉ፡፡ ሁለቱ ደራሲያን የዚያን ዘመን እና የዚያን ትውልድ ግብር እና ገቢር በየፊናቸው ከትበውታል፡፡ ሕይወት Tower in the Sky ብላ ጻፈች፡፡ አዳም “ይወስዳል መንገድ ያመጣል መንገድ”ን ጻፈ፡፡ በነዚህ ሁለት ድርሳናት ውስጥ አጮልቄ አየሁ፡፡ ተመሳስሎው ይገርማል፡፡ ያንን ዘመን ከፖለቲካው ምሽግ ሳይሆን ከሰው (ከተራ ሰው) አንጻር ተርከውታል፡፡ ‹‹ተራ›› የሚለው ቃል አሉታዊ ትርጓሜውን እርሱት፡፡ Tower in the Sky ሲጀምር ይህች ውብ ጥቅስ አለች፤ “To speak of this is painful for me: to keep silence is no less pain. On every side is suffering” ይህ የሕይወት የኑዛዜ መክፈቻ ይመስለኛል፡፡
በ”ይወስዳል መንገድ ያመጣል መንገድ” መጨረሻ ላይ ደግሞ አለሙ እንዲህ ይላል፤ ‹‹ፊት ለፊቴ ገና የምሰርዘው ጥቁር ትዝታ አለ፡፡›› ልብ በሉ፤ ጥቁር ትዝታውን የሚሰርዘው በኑዛዜው ነው፤ ‹‹ከመናዘዝ የበለጠ ላጲስ የት አለ?›› እንዲል፡፡ ‹‹ያቺ¸ ቢጫ ነቁጥ የየራሱ ኑዛዜ ናት፡፡›› ሁለት ኑዛዜዎች (ኑዛዜያት . . . ?) ዘመነ ንጽህና አዳም (በአለሙ በኩል) እና ሕይወት ኑዛዜያቸውን የሚከትቡት ዕንባቸውን እያጠቀሱ ይመስለኛል፡፡ ለከሸፈ ሕልማቸው፣ ለሞተ ፍቅራቸው፣ ለተበረዘ ንጽህናቸው፡፡ የሕይወት መጽሀፍ የመጀመርያ ክፍል፣ በአዳም አንደኛዋ ጎዳና ይመሰላል፡፡ ባጭሩ ሁሉ ነገር ንጹህ ነበር፡፡ በቃ! (የሚናፈቅ ንጽህና) (የጠፋ ንጽህና?) እየሄድን ነው . . . . ዘመነ ንቃት (‹‹ነገን ፈርተህ አትተኛ››) ንቃቱ ሲጀመር ቀላል ነበር፡፡ ከርዕዮተ ዓለም ይልቅ የማርክሲስት ቃላትን ማንቸልቸል የ‹‹ንቃት›› እና የ‹‹ዕድገት›› ምልክት ነበርና... ከዚያ ያለፈ ዓለም፣ ከዚያ ያለፈ ዓላማም አልነበረም፡፡ ነገሮች መለዋወጥ ሲጀምሩ (የአብዮት ነፋስ ሲነፍስ ይሉታል) ወደ ፖለቲካው ጠጋ ጠጋ ማለት ይጀመራል፡፡ ሕይወት በጌታቸው ትማረካለች (ትመለመላለች) አለሙ ደግሞ በእነገብረወልድ፤ ‹‹ገብረወልድን የተዋወቅሁት እዚህ ነው፡፡ ቅዱስ ከተባለ አራዳ ጋር የተዋወቅሁት እዚህ ነው፡፡ መንግስት ገልባጭ ለመሆን የተመለመልኩት እንትና ካፌ ቤት ገብረወልድ የገዛልኝን ቺዝ በርገር በቡና በወተት እያማግሁ ነው፡፡›› ይላል አዳም፡፡
ሕይወትም እንዲሁ ነች፤ ሐረር ምግብ ቤት! እና... የጓዶች ቤት... የፖለቲካን ሀሁ እንደዋዛ የቀሰመችው፡፡ የማርክሲስት ቃላትን እንደ ዋዛ ከማንቸልቸል፤ ፖለቲካን ወደ ማብሰልሰል ከፍ ሲባል፤ ‹‹ቀልዱ ቀልድ አልነበረም›› የፖለቲካው ትኩሳት በማንነት ውስጥ መብላላት ሲጀምር ወሰን አልባ ሕልም ይታለማል፡፡ ጽንፍ አልባ ዕቅድ ይታቀዳል፡፡ አዳም አንድ ጎዳናው ላይ ሆኖ እንዲህ ይላል፤ ‹‹ዓይኖቻችንን አድማስ ስፌት ላይ ተክለን ትዕንግርት ባልገባው የልጅነት ልባችን ትዕንግርት ልንሰራ የፈለግነው እዚህ ነው፡፡›› አድማስ ስፌት ላይ አይኖቻቸውን ተክለው ሊሰሩት ያሰቡትን ትዕንግርት ሕይወት ባጭሩ እንዲህ ትለዋለች፤ ‹‹Tower in the Sky! ›› ዘመነ ለውጥ ለመኖር ምክኒያት ያስፈልጋል፡፡ ለመኖር ሕልም ያስፈልጋል፡፡ የዚያ ዘመን ሕልም ለውጥ ነበር፡፡ ይህ ሕልም መንገድ ይቀይራል፡፡
ሕይወት ይቀይራል፡፡ ትምህርትም ትረሳለች፡፡ (በአዳም ቋንቋ ሳይንስ ታመልጣለች፡፡) “Perusing my education seemed selfish and inconsequential in light of the plight of the masses that needed to be lifted out of poverty. What was education when the people needed me?” - Tower in the sky ‹‹ሕዝብ እየተጨቆነ መማር ምን ይሰራል! የጎጃም፣ የባሌ፣ የኤርትራ ገበሬዎችና የአምቦ ተማሪዎች እየተጨፈጨፉ... ጎጃም ያለቀ፣ ባሌ የተደመሰሰ፣ አምቦ የተቃጠለች መሰለኝ፡፡›› - ይወስዳል መንገድ ያመጣል መንገድ፡፡ እንቀጥል፤ ባቡሩ እየተጓዘ ነው፤ የፖለቲካው ስሜትና ዕውቀት፣ አቋም ይወልዳል፤ ያውም ጠንካራ አቋም፡፡ የለውጥ አማራጭን የሚቀይስ ሕቡዕ አቋም፡፡
ይህ አቋም ባደባባይ ሲገለጥ እንዲህ ነበር፡፡ “The entire city was submerged in a sea of red with banners hoisted everywhere and walls ornamented with slogans. The graffiti and banners were as much the delight of members as they were Derg’s nightmare.” Tower in the sky ‹‹አጥሮች ላይ፣ ግንቦች ላይ፣ ጣውላዎች ላይ፣ ቆርቆሮዎች ላይ በሚንቦጎቦግ ደማቄ ቀለም፤ ‹‹ሕዝባዊ መንግስት በአስቸኳይ!›› ‹‹ኢህአፓ ያቸንፋል›› እየተባለ የሚጻፈውን አንብቤ በቡድኔ ስፋት የኮራሁት እዚህ ነው፡፡ ከሚሊዮን አመታት በፊት በሴኖዞይ ክፍለ ዘመን ከተፈጠረው የሀገሬ አፈር ገነው የሚያበሩ መፈክሮች ያየሁት እዚህ ነው፡፡›› ይወስዳል መንገድያ መጣል መንገድ፡፡ እዚህ ጋ ማን ምን እንደሆነ ታውቋል፡፡ ጠላትነት እዚህ ተጠንስሷል፡፡ ጎራው ተለይቷል፡፡ ‹‹መንገዳችን ለየቅል ነው›› ያሉ ሁሉ በየፊናቸው ይመሽጋሉ፡፡ ልጅነት፣ አብሮነት እና ንጹህነት በፖለቲካ ይሰረዛል፤ የልጅነት ፍቅርም እንዲሁ፡፡ (ለበጎም ሆነ ለክፉ) ‹‹አብሮ ማደግን ፉርሽ አደረግናት፡፡ በልጅነቴ በሰበሰብኩት ዕውቀትና መታመን ገበና በማወቄ ሳራን አስገድያለሁ፣ ካሱን አሰቅያለሁ... አብሮ አደጋችንን የሚያስከነዳ አዲስ የሩቅ ጓደኛ የምንተዋወቀው እዚህ ነው፡፡›› - ይወስዳል መንገድ ያመጣል መንገድ “To my surprise, it was the friends I grew up with that I had difficulty understanding any longer. I could feel an abyss separating us. . . . It was my comrades for whom my heart leapt every time” – Tower in the sky ይሄኔ መራሩ ዕውነት ማቆጥቆጥ ይጀምራል፡፡ ንጽህናው ሲበረዝ... ‹መቸሻቸሽ› ይቀጥላል፡፡
ደም! መለየት፣ ሞት... የሚወዱትን ማጣት ጌታቸው አልፏል፣ ደበበ ሄዷል፣ መሪማ ‹አርጋለች› ባመኑት ሰው መሞት የዘመኑ ቀለም ነበር፡፡ ‹‹ለምን ሞተ ቢሉ...›› “What did he die for? For trying to save lives? Is all this in the name of the revolution... in the name of the people? Are we justified to do away with peoples’ lives in the name of the revolution?” – Tower in the Sky ‹‹መሞት ሳያስፈልገኝ ሙት አሉኝ፡፡ መሬቱን የወሰደ ገበሬ ቀኑ አልፎለት ሳላይ ከጀርባዬ እየነዱ አቻኮሉኝ፡፡ በትግል እንጂ በአዋጅ መሬት አይሰጥም ብለው፡፡ ሞቴን ወደ ሰበበኝነት ፈጠሩት፡፡›› - ይወስዳል መንገድ ያመጣል መንገድ፡፡›› ጥያቄው ከባድ ነው፡፡ ያማል፡፡ ልብ ያደማል፡፡ ፍቅር፣ ትግል፣ ሰው! ሰው፣ ፍቅር፣ ትግል! ትግል፣ ፍቅር፣ ሰው! . . . . . . ውዥንብር! ዘመነ አስተውሎት ሀዘን በወለደው ስሜት ነገሩሁሉ . . . . ግራ ቀኙ ሲታይ . . . . አስተውሎት (Realization) ይከተላል፡፡ አዳም Czaykowski Bodgan የተባለ ጸሀፊ “Put your hands in the flame if you are a man” ያለው ላይ ተንተርሶ እንዲህ ይላል፤ ‹‹ወንድ ስለሆንኩ እጆቼን ነበልባል ውስጥ ጨመርኩ፡፡
ታዲያ ብርሀን ሳይሆን አንጀቴ ውስጥ ጠማማ ቁስል ቀረ፡፡›› ‹‹But, like Icarus, who flew too close to the sun and got the wings of his chariot burned, it came too close to the “Sun” for its own good too.” Tower in the Sky ግዜ ያልፋል፡፡ ነገሮች ተቀያይረው . . . የሞት ዕጣ ለሁሉ እየተዳረሰ . . . እሳቱ የበላቸው እያለፉ . . . የተረፉትም . . . ስደት!! ሕይወት እንዲህ ትላለች፤ “ . . . Others flooded European and North American cities. Wherever they lived, many of them became eternal strangers to the world and to themselves. Devoid of dreams and ideals, they lost meaning in the present or the future” ‹‹የለንደን መንገዶች አስፋልትና ሲሚንቶ ናቸው፡፡ አላውቃቸውም አያውቁኝም፡፡ የትኛውንም ቦርቡሬ ገበጣ መጫወት አልችልም፡፡ ሱፐርማርኬቱን ከላይ እስከ ታች በላስቲክና በክርታስ የተጠረዘ ምግብ ሞልቶታል... ሁሉ ነገር አዲስ ነው፡፡ እዚህ ለተወለዱትም ሁሉነገር በየቀኑ እንግዳ ነው... አዲስ ነገር አልፈራም ግንትር ጉሙን ፍለጋ እማስናለሁ፡፡›› ከዚህ ሁሉ የተረፈው ማንነት በእስር፣ በዕድሜ ሲሞረድ .... ትላንት ቁልጭ ብላ ስትታይ... (አለሙ በጠባብ ቤት ውስጥ... ሕይወት በጠባብ እስር ቤት) ራስን መመርመር ይከተላል፡፡
‹‹በዚህ መንገድ አልፌ ነበር? በዚህ መንገድ መጥቼ ነበር? እላለሁ፡፡ ልላቸውም እፈልጋለሁ፡፡ እንደምትወዱኝ ሁሉ ከልጅነቴ አትሟጨጩ፣ ከልጅነቴ ምን አላችሁ? ልጅነቴን ብትኖሩብኝም፣ ማስታወሴና ትውስታዬን መተርጎሜ ግን ዛሬ የኔ ናት›› ይወስዳል መንገድ ያመጣል መንገድ፡፡ ‹‹Slowly, I felt a new person surging in me. I gained confidence in the knowledge that I can define and redefine myself. I could determine who I wanted to be and where I wanted to go.” – Tower in the Sky ይህ ምርምር ከ‹‹እኛ›› ውስጥ ‹‹እኔ›› የሚባል አዲስ ማንነት ይፈጥራል፡፡ “Why do people imitate others? Why do they follow them blindly? . . . Will I ever belong to a group again” – Tower in the Sky አዳምም በተዋሳቸው ስንኞች፤ ‹‹የወል ልቦናችን የጋራ ልባችን አደረገን ባዶ የግሉን ልቦና የግሉን ልብ ወስዶ፡፡›› ይላል፡፡ ዘመነ ንስሀ ፍጻሜው ሲቃረብ “. . . I always wanted to emulate: respect for human life, tolerance and peaceful resolution of conflict” – Tower in the Sky “ይሄ ጎዳና የይቅርታ ነው፡፡ ሁለት እግሮቼን አገጣጥሜ የምቆምባት ሰንበሌጥ መንገድ አለች፡፡ ቦታዬ አለም ይመስለኝ ነበር፡፡ ቦታዬ ግን ይህቺ ናት፡፡›› - ይወስዳል መንገድ ያመጣል መንገድ ‹‹ሕይወት›› - ‹‹ሰው›› - ‹‹አዳም›› ዕውነት ዕውነት ነው፡፡

ሳለ-ለሌለ
እየታለ. . .እየተሌለ
በመሸ-ነጋ-መሸ
  እንደነበረ. . .እንዳለ
እንዳደረ. . .እንደ-ዋለ
  እንዲሁ. . .
እንደ-ዋተተ
 «መኖር» እንደ-ሞገተ
«ኗሪ» ሳይኖር. . .
 ኖረ. . .ኖረና-ሞተ፡፡
ተኖረ-ተኖረና፣ተሞተ
 ተሞተና-ተለቀሰ
ዕንባ እንደ ጅረት ፈሰሰ
 ደረት-እንዳፈር ፈረሰ
ምድረ ቡትቷም. . . ርንቁስ-ደሀ!
ተቃቀፈና አነባ!
ለማንም. . .ምንም. . .ላይረባ!
ግና!. . .ያረፈ
እንዳላረፈ. . .አረፈ
አየ. . .አየና-አለፈ፡፡
«ትቢያ» ነበር «ትቢያ
             ለበሰ
ለሟች-ኗሪ. . .
   ለኗሪ ሟች. . .ወግ ደረሰ!
            / ክፍሌ አቦቸር



በራስ ላይ ፍርድ መስጠት
በየካቲት ከጋይንት ተሰሪ አግብተው ሳለ ወታደር ባላገሩን ገደለው፡፡ የሞተበት ሰው ከንጉሡ መጥቶ ጮኸ፡፡ ንጉስ ቴዎድሮስም ወታደሩን ሁሉ አፈርሳታ አውጣ አሉት፡፡ ወታደሩም አልገደልነም አላየንም ብሎ በተገዘተ ጊዜ፣ ለንጉሥ ቴዎድሮስ ይህ ነገር ጭንቅ ሆነ፡፡ አስበውም ኋላ እንዲህ አሉ፡- ወታደር ብላ ባላገር አብላ ያልሁ እኔ ነኝና ደመኛህ፣ እኔን ግደል ባሉት ጊዜ ባለደሙም እኔ ንጉሥ መግደል አይቻለኝም አለ፡፡ ንጉሡም ብዙ ብር ሰጥተው ሰደዱት፡፡
/ ኢኖ ሊትመን፣«የቴዎድሮስ ታሪክ» 1902 .








ልክፍተ-አዳም                በእዮብ ምህረትአብ
*

*
መቼም ስለ አዳም ረታ ስራዎች ለመቅደድ የደፈርሁት፣ ‘እስቲ ስለ አዳም ስራዎች የሚሰማህን ስሜት ከኛ ጋር አብረህ ግለጽ’ ተብዬ ተጋብዤ ነው፣ በAdam Reta Group.

በዛ፡-ከኦሮማይዋ ፊያሜታ፣ ከሰመመኑ አቤል፣ ከትኩሳቱ ባህራም ጋራ ተዛምጄ ሌላ ዘመድ ባጣሁበት፤ በዛ “ኧረ አዲስ የአማርኛ ልብ ወለድ ጠፋ!” ባልኩበት፤ በዛ ‘አድጌያለው’ ብዬ ልበ-ወለድ ጽሁፍን ማንበብ እርግፍ አድርጌ በተውኩበት፤ በዛ ስራ ተኮር የእንግሊዘኛ መጽሀፎችን እና እነ TIMEን Newsweekን ማሳደድ በጀመርኩበት ዘመን፣ በዛ. . . . . ከ’ለታት ባንዱ ቀን ወደ Book World ጎራ አልኩኝ፡፡ ‘ግራጫ ቃጭሎች’ የሚል መጽሀፍ በ30 ብር ገዝቼ ወጣው፡፡

መጽሀፉን የገዛሁት ስለዝናው ሰምቼ ሳይሆን ገለጥ ገለጥ ሳደርገው በቀይ ቀለም የተጻፉ ቃላቶችን ሳይ፣ ‘ሰውየው/ደራሲው ተራቃቂ freak ሳይሆን አይቀርም’ ብዬ ተስቤ ነው፡፡

አነበብኹት፡፡

መጀመሪያ:-ጠላሁት(‘እንጀራ’ ምናምን እያለ ይዘበዝባል)

ቀጥሎ:- እንደ መደበሪያ ገፋሁበት (አሁንም ጥልቀቱ አሰለቸኝ)

ቀጥሎ፣ ቀጥሎ- ትንሽ እየሳበኝ መጣ (መዝገቡ የተባለችው ወዝጋባ ጩጬ ትገርመኝ ጀመር)

ቀጥሎ፣ ቀጥሎ፣ ቀጥሎ-ወደድኩት

ቀጥሎ፣ ቀጥሎ፣ ቀጥሎ፣ ቀጥሎ፣ ተቀጣጥሎ፣ ቀጥሎ፣ ቀጥሎ፣ ቀጣጥሎ፡-(እሱን Part ማውራት ማሽቋለጥ ይመስላል፣ እንዝለለው)

***

(አሁን)

የአዳም ረታን ስራዎች እንዲህ እንዲህ ብዬ የማልገመግምልህ ልኬን ስለማውቀው ነው፡፡

ካልሆነማ፡

የማንም ልቅምቅም

የሰው ልክ አያውቅም

. . . . . . . . .ቢያውቅም

በደንብ አይጠነቀቅም . . . . . . . . . . . .የሚለው የኛ ሰፈር indigenous ግጥም እኔን በትክክል ሊገልጽ ነው፡፡

***

***
ግን እንደው ባጠቃላይ የአዳም ረታ ስራዎች ለኔ ምን ማለት እንደሆኑ በቀላል አማርኛ እና በወረደ ማስረጃ ልንገርህ፡፡ ከልቤ ነው፡፡

(አንድ)

በሆነ አጋጣሚ ከእንግዳ ሰው ጋር ሰው ትተዋወቃለህ፡፡ እየተግባባኸው ስትሄድ የወሬውን wave length መለካት ትጀምራለህ፣ ከዛም እንደሰውየው ሙድ ትቀዳለህ፣ ወይንም ታዳምጠዋለህ፡፡ እውቀት ነገር መቅደድ ከጀመረና ከመሰጠኝ ግን እንደቀልድ “የአዳምን ስራዎች አንብበህ ታውቃለህ ወይ?” ብዬ እጠይቀዋለው፡፡”አላውቅም/ ስሙን ሰምቼ አውቃለው/ አንድ መጽሃፉን ብቻ አንብቤለታለው” ምናምን ካለኝ፣ ግልግል ነው፡፡ የአወራሩን ጌጅ (Gauge) ወደመሬት አውርጄ ጉዳይ ካለን ጉዳያችንን፣ ጉዳይ ከሌለን ደግሞ ስለ ገጠመኙ፣ ስለ ስራው፣ ስለ ከተማው ትኩስ ፉገራዎች ወዘተ.. አዋራውና አመልጣለው፡፡

ግን ደግሞ “አንብበሃቸዋል ወይ?” ስለው፡ “ያምሃል እንዴ?!”፤ “እንዴት ነው የማላነባቸው?!”፣ “ምን ማለትህ ነው?!” ካለኝ አለቀ! ከሰውየው ጋር ሰፋፊ ideaዎች መበልጠጥ ይቻላል ማለት ነው፡፡ አልፋታውም! . . . ወይ እንደ እብድ ስለአዳም በስሜት እንቀዳለን፣ ወይንም ሌላነገር በተመሳሳይ ጡዘት እንቀዳለን፡፡

(ሁለት)

በህይወት ዘመኔ በፌስቡክ ተዋውቀን ስልክ ተቀይይረን በአካል ያገኘኋቸው ሰዎች 6 ናቸው፤ (ሶስቱ ሴቶች ሶስቱ ወንዶች)፡፡ ስድስቱም ማወቅ/ እውቀት ይወሰውሳቸዋል፣ ስድስቱም አዳምን አንብበዋል፣ ከአንዷ በስተቀር ከአምስቱም ጋር በተገናኘንባቸው ግዜያት ስለ አዳም ስራዎች ለፍልፈናል፣ በስሜት ‘ኡኡ!’ ብለናል፣ ተናብበናል፡፡

አንደኔ ልክፍተ-አዳም ያደረብህ ጀለሴ፣ በቁም ነገር ፍቅረኛ ከጠበስክ፣ ቀድመህ የአዳምን ስራዎች ማንበቧን ቼክ አድርግ፡፡ ካልሆነ እንጃ፡፡ ኋላ አስሬ፡ “አዳም አዳም” ስትላት፡ “ደግሞ ጀመረህ!” እንዳትልህ፡፡

(ሶስት)

ብዙ ግዜ እንቅልፍ እምቢ ሲለኝ፣ የአዳምን መጽሀፍ አነሳና ዝም ብዬ ከመሀል ጀምሬ አንዱን ታሪክ አነባለው፣ ከዛም በimagination እያጦዝኳቸው አብሬአቸው እደቅሳለው፣ ከገጸባህሪይቶቹ ጋራ፡፡

***

ወንድሜ ያዕቆብ ሆይ፣ በውኑ ዔሳው ወንድምህ በአዳም ከዚህ በላይ ሊለከፍ ይችላልን????

. . . ናና ከረሜላን፣ ወሰን የለሽን፣ ያችን ጉብታ፣ አበበ ቢቂላን፣ ሙስጠፋን፣ ‘እእ’ን፣ ገነትን፣ ‘ጨረቃ ስትወጣ’ን፣ መርሳትስ ይቻልሃልን??

***

***

(አሁን ከህይወትህ ጋር የሚሄድ ወሬ ላውራልህ)

የኣማርኛ መጽሃፍ ካነበብክ ቆየህ፣ ወይንም ደግሞ ኮሌጅ ከጨረስክ ጀምሮ ልብወለድ ማንበብ አቁመሃል ብዬ ልጠርጥርህ፡፡ አይገርምም፣ ብዙ ሰው እንደዛ ነው፡፡

ግን ግን ግን ግን

ምንም ቢሆን ምንም አዳም ረታ ስራዎችን አለማንበብ ካንተ በፍጹም አይጠበቅም፡፡ካላመንከኝ አሁኑኑ ያ ማንበብ በጣም የሚወደውን የድሮ ጀለስህን ደውለህ ስለ አዳም ረታ ጠይቀው፡፡ ‘ኡኡ’ እያለ ያወራሃል፡፡

እንደው ምናልባት እስካሁን የአዳምን ስራዎች አንብቤ አላውቅም ካልክ ርእሳቸውን ልንገርህና እስቲ አንዱን ሞክረው፡፡ ሱሴ ነገር ይሆኑብሀል፡፡ የተወሰኑት ገበያ ላይ አሉ፡፡ የተወሰኑት ጠፍተዋል፡፡

1. ማህሌት
2. ግራጫ ቃጭሎች
3. እቴሜቴ ሎሚሽታ( አሪፍ ፊልም ተሰርቶበታል)
4. አለንጋና ምስር
5. ከሰማይ የወረደ ፍርፍር
6. ይወስዳል መንገድ ያመጣል መንገድ
7. ህማማትና በገና

***

(በነገራችን ላይ Adam Reta Group የአዳምን ቃለ መጠይቆች ጨምሮ ብዙ ሰፊና ጠቃሚነገሮች አሉት፡፡ የዝች አገር Brilliant በሙሉ አባል ነው( ገብተህ ስማቸውን እየው) እስካሁን ኣባል ካልሆንክ አሁኑኑ ግባና የእስካሁኑን ጽሁፎች ኮምኩም፤ ቀላል ታተርፋለህ!

(ደግሞ Surprise ሊያደርጉን ተዘጋጅተዋል:-ሚስጥር ነው)

***

የአዳምን ስራዎች አንብበህ ግን ‘ሎሚ ሽታ’ የተሰኘውን በአዳም ድርሰት ላይ የተሰራውን ፀዴ ፊም እስካሁን ካላየህ፣ አሁንም እድል አለህ፤ ከሲኒማ ቤት አልወረደም፡፡

አርብ 10 እና 12 ሰአት ላይ በአምባሳደር ሲኒማ፣
ሀሙስ 11 ሰአት ላይ በ ሲኒማ አምፒር፣ እንዲሁም፣
አርብ 12 ሰአት ላይ በራስ ሆቴል ይታያሉ ያሉት

*

*

አዳም ሆይ፣

ኑር!
. . . በቃ፣ ዝም ብለህ ኑር!

ብትጽፍም ባትጽፍም. . . .ኑር . . አንተ ብቻ ኑር!

ኑርልኝ!!

*

*
አክባሪህ፣

እዮብ ምህረትአብ








የበሃይሉ ሽሙጦችና ፖለቲካችን ! Written by  ደረጀ በላይነህ

ብዙ ጊዜ ቀልድ የምጠብቀው ከተደላደለ ህይወት፣ከሚጣፍጥ እንጀራ መሶብ እንጂ ከመረረ የኑሮ ዉጣ ውረድ አይደለም፤ግን ተሳስተናል፡፡ ብዙ ታላላቅ ደራሲያን የተወለዱት በጦርነትና በሰቆቃ ማህጸን እንጂ በተድላ አበባ እምብርት ላይ አይደለም። ንቦች ናቸው ከጥሩ መዓዛ ማር የሚጋግሩት፡፡ ንቦች ስል የኛን አገር ንቦች(ኢህአዴግን)ማለቴ አይደለም፡፡ በቅርቡ ያነበብኩት፡፡ ግን ደግሞ ትንሽ ቆየት ያለ (በ2001) የታተመ መጽሃፍ “ድህነት” በእንግሊዝኛው “poverty”ብሎ የጻፈው ጽሁፍ የሚያሳዝንና የሚያስቅ ነበረ - ጆ ጉድ ዊን ፓርከር፡፡ “Poverty is being tired. I always been tired. They told me at the hospital when the last baby came that I had chronic anemia caused from poor diet, a bad cause of worms, and that I needed a corrective operation. I listened politely – the poor are always polite. The poor always listen.”
ድህነት ሁልጊዜ በመከራ ላይ መከራ ያደከመው ነው፡፡ ድሃ ሁልጊዜ አንገት ደፊ፣ ሁልጊዜ አድማጭ ነው፡፡---ጸሃፊው ብዙ ቀልድ ይቀልዳል፡፡ ምክንያቱም ዘፋኙ እንዳለው መናደድ ሲበዛ ያስቃልና!... የዛሬው ርዕሰ ጉዳዬ፣ የበኀይሉ ገ/እግዚአብሄር “ኑሮ እና ፖለቲካ” የተሰኘ መጽሃፉ (በቅርብ ቁ- 2 ብሎ ያወጣው) ውስጥ ያሉ ቀልዶች ናቸው፡፡ በ160 ገጾች የተካተቱት የበሃይሉ ቀልዶች ሙሉ በሙሉ ከሃገራችን ፖለቲካ ጋር የተያያዙ ስለሆኑ ብዙ የረሳናቸውን ነገሮች ያስታውሱናል፡፡ እያዋዙ ታሪክ ይነግሩናል፡፡ በጣም ያሽሟጥጣሉ፡፡ ከንፈራቸውን እያወዛወዙ፡፡ በተለይ የምርጫ 97 ስህተቶችና ነውሮችን ያሳዩናል፡፡ እስቲ ትንሽ እንይ፡- አቅመ ደካማዋ ባልቴት ወ/ሮ ልጓሜ በ1997 ዓ.ም የተካሄደውን ብሄራዊ ምርጫ ተከትሎ በተነሳው ብጥብጥ “ድንጋይ ወረወረ” ተብሎ በጠገበ ቆመጥ በፀጥታ ሃይሎች የተሰባበረ ጎረምሳ ልጃቸውን እያስታመሙ ነው፡፡ ታዲያ በዚህ መሃል በቴሌቪዥን፣ የህገ መንግስት ጥያቄና መልስ የሞባይል ካርድ የሚያሸልም ጥያቄ ይጠየቃል፡፡ ”በፓርላሜንታዊ ስርዓት የሃገር መከላከያ ሰራዊት ተጠሪነቱ ለማን ነው” የሚል ነበር፡፡ ይሄኔ በጋቢ ተጠቅልሎ የተኛው ልጅ፣ ጥያቄውን ለመመለስ ሞባይሌን አቀብዪኝ - ይላል እናቱን፡፡ እናትየው “አይ ልጄ ድከም ብሎህ እኮ ነው፤አሁን የዚህ ጥያቄ መልስ ሰው ይጠፋዋል ብለህ ነው
” ልጁም መልሶ “እስቲ ካወቅሽው መልሱ ምንድነው?” “ጥያቄው የመከላከያ ሰራዊቱ ተጠሪነቱ ለማነው? ነው አይደል?” “አዎ!” “ለዲያቢሎስ ነዋ ሌላ ለማን ይሆናል?”አሉ እትዬ ልጓሜ - በፀጥታ ሃይሎች የተሰባበረ ልጃቸውን በብስጭት እያዩ፡፡ ይህ የ1997 ዓ.ም ምርጫ በታሪካችን እጅግ አስገራሚና ለውጥ የናፈቀ እንደ ነበር ሁላችንም የምናስታውሰው ስለሆነ ይህን ጉዳይ ማንሳቱ የግድ ነው፡፡ ዛሬ ዛሬ በሚደረጉት ምርጫዎች ላይ በሰላም ተጠናቀቀ፤ ወዘተ ሲባል ያስቀኛል፡፡ ሆዳችን እያወቀው ለምን እንደምንሸዋወድ አይገባኝም፡፡ መንግስት የምናውቀውን ነገር እየዋሸ ከሚያበሳጨን ምናለ ዝም ብሎ የወደደውን ሳያወራ ቢያደርግ! ... ለመሆኑ የትኛው መነሳሳት ነው ረብሻ የሚያስነሳው! ... ኢህአዴግ ከራሱ ጋር ሊጣላ ነው! ...... ኩመካ ይመስላል፡፡ እንደኔ እንደኔ ኢህአዴግ ከራሱ ሰዎች ለመምረጥ ካልሆነ በቀር ምርጫ የሚባል ነገር እየመጣ ባያበሳጨን! ... ኢህአዴግ በፈጠረህ አርፈህ ግድቡን ጨርስ … ባቡሩን ቶሎ ቶሎ አሰራ!...ብሎ የሚነግርልኝ ቢኖር ደስታውን አልችለውም፡፡
ከበኃይሉ መፅሐፍ ዘና ለማለት ያህል “ውዴ የትም አትጠብቂኝ” የሚለውን ትንሽ እንየው ይሆን!.. ”ፒያሳ መሃሙድ ጋ ጠብቂኝ ፤ ቦሌ ፒኮክ ጋ ጠብቂኝ ፤ መርካቶ ምዕራብ ሆቴል ጋ ጠብቂኝ ፤ አራት ኪሎ ጆሊ ባር ጋ ጠብቂኝ ፤ ሽሮሜዳ መዶሻ ጠጅ ቤት ጋ ጠብቂኝ ---- የደላቸው ይባባሉ፡፡ ውዴ እኔ ግን እላለሁ፤ የትም አትጠብቂኝ! እንድትሰሚ? ምን እንድትጠጪ? ምን እንድትበዪ?… ጉድ እኮ ነው! ውዴ! እነሱ ወገኞች ናቸው፡፡ ፒያሳ፣ ቦሌ፣ መርካቶ---ሲባባሉ አንዳች የሚታይ ተዐምር አለ ብለሽ እንዳትጠብቂ፡፡ በዛም ብትሄጂ በዚህ፣ ጠጅ ቤት ገባሽ ድራፍት ቤት፣ ቡቲክ ደጃፍ ላይ ቆምሽ፣ ጫት መሸጫ ሱቅ ፤ ጭድ ተራ ወረድሽ፣ ጎማ ተራ፤ የሚታየው፣ የሚሰማው፣ የሚተነፈሰው ሁሉ የማያምርበት፤ ከቀልቡ ያልሆነ ህዝብ ወዲያና ወዲህ የሚልበት ነው፤/አይ ውዴ ቀልብ ከሌለ ቀልብ ከየት ይመጣል አልሽ!?…ሕም!/ “ፒያሳን ያየሽው እንደሆነ…/ለነገሩ ምኑ ይታያል?/ አካል ጉዳትና እግዜር የቀማውን አካል ወደ ገቢ ማስገኛ ቀይሮ መሬት ላይ ተነጥፎ ሲለምን ማለፊያ ይነሳሻል፡፡
እናቲቱ ጡቶችዋን ልጆችዋ አፍ ላይ ደቅና ራቁቷን አስፓልት ላይ ተቀምጣ እንቅፋት ትሆንብሻለች፡፡ ጎረምሳው ከፒያሳ የሚሰፋ እጁን ፊትሽ ላይ ዘርግቶ ዛቻ እና ማስፈራሪያ በተቀላቀለበት ማጉረምረም፣ “ራበኝ፤ አምስት ብር አምጪ!” ሲል ያስደነግጥሻል፡፡ /እንዴ! ብራችን የሚጀምረው ከአምስት ብር ሆነ እንዴ/ “ኧረ እኔም ከነጋ እህል በአፌ አልዞረም!” ካልሽው፤ እጅሽን ቀብ አድርጎ፣ “ራበኝ!” ይልሻል በድጋሚ አይኑን አፍጥጦ፡፡ “ካልሰጠሽኝ ዋ!” መሆኑ ነው፡፡/ በእህል ውሃ የምንቀረጠው አንሶ ለእግዚሃሩ አየርም ቅረጡ ሊሉን ነው እንዴ፡፡ እግዝኦ! በዚህ ደካማ አቅማችን የተሸከምናቸው አነስተኛና ጥቃቅን መንግስታት መብዛታቸው!/ በነገራችን ላይ ውዴ፤ ሁለት ልጆችዋ አፍ ላይ ጡትዋን ደግና ወደምትለምነው እናት ልመልስሽና ልጆቹ ጡት እየጠቡ ይሁን ገቢ ማስገኛ ቴአትር እየተጫወቱ በውል ማወቅ አልቻልኩም፡፡” በዚህ ርዕስ ላይ የጻፈው ትዝብትና ሽሙጥ ይቀጥላል፡፡ ከላይ የጠቀስናቸውን መጽሃፍት የሚታዘብ፣ ወይም ለቀልድ የመረጣቸው ይመስላል። መጽሃፉ ብዙ ጉድ አለው፡፡ “ኣያዋጣኝም!” ይህ ታሪክ የኮንዶሚኒየም ዕጣ ሲወጣ ለማየት የፈለገ ጓደኛው፣ ተራኪውን ወደ ቤት አጣድፎ ከወሰደው በኋላ ያለውን ሁኔታ ነው፡፡ እስቲ እንየው፡- “እዚህ ላይ ሁል ጊዜ የሚገርመኝ የኤርትራ ቴሌቪዥን ፣የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ሲሠራ የሚሰራ፣ ሲበላሽ አብሮ የመበላሸቱ ነገር ነው፡፡
ነገሩ በስም እና በአገር ቢለያዩ እንጂ በሚያስተላልፉት ፕሮግራምስ አንድ አይነት ናቸው፡፡ እዚያም የሚታረስ መንገድ፤እዚህም የሚታረስ መንገድ፤እዚያም ያማረ የገብስ ማሳ፤እዚህም ያማረ የገብስ ማሳ፡፡ እዚያም “ቶክ ፉት ቦል”፤ እዚህም “ቶክ ፉት ቦል”፡፡ /እንደ አጋጣሚ ሆኖ በኤርትራ ቴሌቪዥን ያላየሁት የኮንዶሚኒየም ዕጣ በቀጥታ ሲወጣ ብቻ ነው/ እንዲህ ያለ ምስስሎሽ ካላቸው ታዲያ ለምንድነው እንደ አልቃይዳ አንዱ ጣቢያ አንዱን ይዞት የሚጠፋው?እንጃ! “ውጪ አገር ያለ አንድ ወዳጄ ሲያጫውተኝ፣ “የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን እንደ ዕድል ሆኖ ሰርቶ ካየሁት ሁልጊዜ እንዲህ እላለሁ” አለ፤”ግን የልማት ዜና አገሬም እያለሁ አይቼዋለሁ፡፡ የገብስ እርሻው ታጭዶ ጎተራ ሲገባ የማየው መቼ ነው? እነዚህስ ሣር የሚግጡ የደለቡ በሬዎች እስካሁን አልታረዱም ካራ ሳይገቡ አረጁ እኮ! ይህስ በአነስተኛ ጥቃቅን ተደራጅቶ አምናም ፣ካቻምናም፣ዘንድሮም ድንጋይ የሚፈልጠው ወጣት፤ ገቢው አድጎ፣ ስራው ተሻሽሎ የማየው መቼ ነው እስከ መቼስ ቱታውን እንደለበሰ፣‹መንግስት ባመቻቸልን የስራ ዕድል ተጠቅሜ ካፒታሌ ይህን ያህል ደርሷል‹ ሲል ይኖራል” ትረካው የኮንዶሚኒየሙ ዕጣ እስኪወጣ ድረስ ያለውን ምጥና ሌሎች ማህበራዊና ፖለቲካዊ ቀውሶቻችንን ያሳያል፡፡ ሌላው ለዛሬ የመረጥኩት “ኑሮዬን ፓርላማ አድርጎታል” የሚለው ነው፡፡ የአንድ ባልና ሚስት ታሪክ ነው፡፡… ሚስት ከምትለው ገባ ብለን እንጀምር፡-“በቃ ምን ልበልህ… ቃላት አጥሯት ድንቅፍቅፍ፡፡ አወዛጋቢው ንግግር ይህ ነው፤ ሚስት፣ “ኑሮዬን ፓርላማ አድርጎታል” ያለችበትን ምክንያት በመጠየቅ ጆሯችንን ለትዳር ብሶት አናጋልጥም፡፡ እንዲህ መጠርጠር ግን እንችላለን፡፡ የጥርጣሬውን ነጥቦች ልለፋቸውና ልቀጥል፡፡ “በስብሰባ ወቅት በመተኛትና በማንኮራፋት ቀሪውን ተሰብሳቢ በመረበሻቸው አራት የፓርላማ አባላት የማስጠንቀቂያ ደብዳቤ ደረሳቸው” ይላል - ዐይኔ ያረፈበት የጋዜጣ ዜና፡፡”አይ ፍትህ! ከፍትህ በታች እንጂ በላይ ማን አለ!? ለመሆኑ ይሄ የሆነው የት ይሆን?”ብዬ በጉምዥት ቁልቁል ሳነብ ጉዳዩ የሆነው ቬትናም የተባለች አገር እንደሆነ ተረዳሁ፡፡
የዛን ሰሞን የኛዎቹ፣”ነፃ ፕሬሶች” ሽወዳ ትዝ አለኝ፡፡”ጠቅላይ ሚኒስትሩ ስልጣናቸውን ለቀቁ!” ብለው በትልቅ ርዕስ ፊት ለፊት ጽፈው ያስነበቡንና፣ ወደ ውስጥ ስንገባ ግን የሌላ እድለኛ አገር ጠቅላይ ሚኒስትር ሆኖ ይገኛል፡፡ ኧረ ሌላም አለ፤ለምሳሌ እቤቴ እስካሁን ያለ አንድ የግል ጋዜጣ ፣”ጠቅላይ ሚኒስትራችን በነገው ዕለት ስልጣናቸውን ይለቃሉ” ብሎ ጽፏል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትራችን ግን ስልጣናቸው ላይ ኖረው በቅርቡ ነው በሞት የተለዩን፡፡ የበኃይሉ ሽሙጦችና ቀልዶች ማህበራዊና ፖለቲካዊ ሂሶችን እንዲሁም ስነ ልቦናዊ ችግሮቻችንን አጣፍጠው የሚያክኩን ናቸው፡፡ መንግስትን…ፕሬሱን …እኛን ሁላችንን እያሳሳቀ ይተቸናል። በተለይ መንግስት መስማት የተሳነው ባይሆን ፤ ከነዚህ ቀልድ መሰል ጽሁፎች በሽታው ምንና የት እንደሆነ ያውቅ ነበር፡፡
ግን አሁን እየባሰበት መጥቶ ጆሮውን በጠጠር ደፍኗል ማለት ይቻላል። ህዝቡን የማይሰማ መንግስት መቼም ቢሆን ጥሩ ስራ አይሰራም፤ቢሰራም ብዙ ከስሮ ነው፡፡ እባክህ መንግስት ሆይ ስማ!! ቅድም ከላይ የጠቀስኳቸው ደራሲ “poverty is asking for help.” ይላል፡፡ መንግስታችን የድሆችን ድምጽ ካልሰማ ለውጥ ይመጣል ብሎ መጠበቅ አይታሰብም፡፡ ሃሳቤን ከማጠናቀቄ በፊት ኢህአዴግ/ኢህዴን/ ካሳተመው “ሶረኔ” የግጥም መጽሃፍ ላይ “የአርሶ አደሮች እንጉርጉሮ” ከሚለው ልውሰድና እኔም እንደ በኃይሉ አሽሟጥጬ ልጨርስ ይሆን? የጭቆና ቀንበር ከብዶ በላያችን በግብር በጉቦ አልቆ ጉልበታችን በጦር በሰፈራ አልቆ ወገናችን መጣልን ኢህአዴግ የነፍስ አባታችን፡፡ ይህንን ግጥም ዛሬ ኢህዴን ሲያነብበው ምን ይል ይሆን?…ታሪክ ይደገማል?… ለጭቆና ታግሎ ጨቋኝ መሆን ጥሩ ነው ትላላችሁ? ኢህአዴጎች፡፡ ወይስ እኔን ትምክህተኛ ትሉኛላችሁ ? ለማንኛውም ልብና ዕድሜ ይስጠን!!

1 comment:

  1. i really loved the comment about adam reta's book and the resemblance you menstioned .that is awsome,keep it up.

    ReplyDelete