Friday, April 26, 2013

አላመሰግንም!!

 እዮብ ምኀረተ አብ
#

#

ተቸገርኩኝ እርዱኝ፣ ካርድ ሙሉልኝ ብዬ አይን አውጥቼ ለምኜ የሞባይል ካርድ ለላካችሁልኝ፣ በተለይም በአካልም ሆነ በስልክ ለማታውቁኝ የCyber ቤተሰቦች፡
በፍጹም አላመሰግንም!!

# # #

በCyberም ቢሆን፣ ብዙም አታቁኝም፤ ስለዚህም ላታምኑኝ ትችላላቹ ብዬ ስማችሁን ታግ ሳላደርግ ለላካችሁልኝ በሙሉ:

አላመሰግንም!

# # #

አየህ; አንዳንዴ ምስጋና ውለታን ያሳንሳል፡፡ ወይንም ደግሞ የተለመደና የወረደ ግብረ መልስ ይመስላል፡፡

ስለዚህም አላመሰግንም፡፡

(እብድ)


ለዛሬ አእምሮው በትክክል መስራት የተሳነው ምናምን አልበል፣ እና እንደተለምዶው እብድ እያልኩኝ እንዳወራ ይፈቀድልኝ፡፡የአእምሮ ጤነኛነት አከራካሪ ነው፡፡ ሁላችንም እብደት አለብን፤ አይነቱ ርዝመቱና ጥለቀቱ ሊለያይ ቢችልም፡፡መቼም በዚህ ውጥንቅጥ በሞላበት አለም ውስጥ ስትኖር አእምሮህ ወጥና ጤነኛ ከሆነ ችግር አለብህ ማለት ነው፣ ወይንም ድንዙዝ ነህ፡፡(ይቅርታ፣ አልያም የምትገርም እድለኛ ነህ)

ካዛንቺስ፣ኦሜድላ ሆቴል ስር ቁጭ ብሎ የሚለምን አንድ እብድ አለ፡፡ቅራቅንቦዎች፣ ጫት ሲጋራና በተለይ ደግሞ የተለያዩ አይነት መድሃኒቶች ፊትለፊቱ ከምሮ የሚለምን፣ ግማሹን ቅርቃኑን የሆነ እብድ፡፡…..እና እንደሌላው ለማኝ ጥበቡን አልተካነበትም፣ዜማና ግጥም ፈጥሮ አይለምንህም፡፡ ወይንም ደግሞ ህጻን እንደታቀፈች ገጠሬ ወጣት ለማኝ ተቅለስልሶና ተቁለጭልቾ አይነ አይንህን አያይህም (ምናልባት አፍራ ይሆናል እንደዛ ምትሆነው)፡፡እሱ ብቻም ሳይሆን አንድ ብር አውጥተህ ስትሰጠው መንጭቆ ይቀበልሃል፤ወይንም ሳንቲም ስትወረውርለት ቀና ብሎ አይቶህ ወዲያው ይዞራል፡፡

እና ካዛንቺስ በተመላለስኩኝ ቁጥር አንድ ብር ሳልሰጠው አልፌ አላቅም (አንድም ቀን!) እንደተለመደው መንጭቆ ይቀበለኛል፣ ፊቴንም በቅጡ አያየውም፡፡ እኔም ብዙም አይገርመኝም፡፡ ግን የአላፊ አግዳሚውን አንጀት ስለማይበላ ሰዉ አያስተውለውም፣ ስለዚህም ሳንቲም አይጥሉለትም ብዬ እያሰብኩኝ ያሳዝነኛል፡፡

(ጠፋው፣ ከካዛንቺስ)

ፊልድ ወጣው፤ ሌላም ሌላም ተጨምሮበት ከካዛንቺስ ለ3 ወር ያህል መሰለኝ ጠፋው፡፡ ከዛ ባለፈው ካዛንቺስ ከሰው ተቀጣጠርኩኝና ተመልሼ መጣው፡፡ እብዱም በቦታው አለ፣ እኔም እንደተለመደው አንድ ብር ልስጥው እጄን ዘረጋሁለት፡፡ አልተቀበለኝም፡፡ ለመጀመሪያ ግዜ አወራኝ!!

(እሱ) “ጠፋህ በሰላም ነው?”

(እኔ፣ ደንግጬ) “አዎ በሰላም ነው”

“ስንት ግዜ እኮ አለፈህ ካየሁህ፣ የታመምክ መስሎኝ… ግን በሰላም ነው?” (ከዛ አጎንብሶ የሆነ ነገር መጎርጎር ጀመረ)

“እንዴት አስታወስከኝ?”

“በጣም ስትጠፋ እኮ የታመምክ መሰለኝ…በሰላም ነው?”….ከዛ መዘባረቅ ጀመረ፣ ሌላ ነገር

“ልብስ ልፈልግልህ ወይ?”

“አልፈልግም! እሸጠዋለው”

“እሺ ምን ላርግልህ?”

የሆነ ነገር አጉረመረመና፣ “ጠፋህ እኮ፣ በሰላም ነው?”

“አለው ደህና ነኝ…በል ቻው” ብዬው ሄድኩኝ፡፡ ቻውም አላለኝም፡፡

# # #

# # #

ይሄ ‘እብድ’፤ ስለኔ መጥፋት የተጨነቀ ‘እብድ’፤ በሰላም ነው ወይ ብሎ ስለኔ ያሰበ ‘እብድ’፤… ልቤ ውስጥ ጠልቆ ቀረ!!!

....ልብስ አልሰጠው ነገር ይሸጠዋል፤ ጫማ አልሰጠው ነገር እንዳይወስዱበትም ፈራው፡፡ደህና ብር አልሰጠው ነገር ያው ነው...

ሰሞኑን ማታ ማታ ሲዘንብ እሱን እያሰብኩኝ በጣም አስብ ጀመር፡፡ እና ቢያንስ መሸፈኛ አሮጌ ላስቲክ (ቤት በለው) ልገዛለት ወሰንኩኝ፡፡ የት እንደሚበላ የት እንደሚውል፣ ሲነጋ ሲመሽ ምን እንሚያደርግ ወዘተ..የቀን ውሎውን ላጠናም ፈለኩኝ፡፡ምን ማድረግ እንዳለብኝ ባላቅም ግን የሆነ ነገር ማድረግ እንደሚገባኝ ተሰማኝ…፡፡

ለዛም ስል፣ ብቻዬን ከምረዳው ቢያንስ Cyber ላይ ለረጅም ግዜ የሚያውቁኝ ሰዎች እንዲያግዙኝ መጠየቅ ፈለኩኝ፡፡አላስፈላጊ የaccountablity ገተታ ከሚፈጠር፣ እንዲሁም ጉዳዩን አካብጄ አውርቼው አጉል ቢሮክራሲ ከሚይዘው፣ ከማሬ ጋር ተማከርን እና ለምን ለኔ ‘የ10 ብር ካርድ ላኩልኝ አልላቸውም?’ ብዬ ይኸው ጠየኳችሁ፡፡

# #

# #

የፈለጣ እርፍና የሚመስለው ይኖራል፣ አራድነት የሚመስለው ይኖራል፣…በኔ አይን አውጣነት የተሳቀቀም አለ፡፡ አልፈርድበትም፣ መብቱ ነው፡፡ጥሩ ያልሆነ ቃልም አይወጣኝም፡፡ግን ደግሞ ይሄን ያህል የሚቸግረኝ ሰው አይደለሁም፣ ወይንም ብቸገርም እንኳ ቤተሰብ እና የልብ ጓደኖች አሉኝ፣ መቼም ሊረዱኝ በቅርቤ ያሉ ማለት የሚያስፈልግ አይመስለኝም፡፡

ግን ግን ግን ግን…ተቸግሬ መስሎት በስልክም በሜሴጅም በፍጥነት ካርድ የላከልኝ አለ፤ አሁን አልቻልኩም ቡሃላ ልላክልህ ያለኝም አለ፡፡እንደ ተስፍሽ ያለው ደግሞ "እዮባ ከምር ከተቸገርክ ከውጭ በሀዋላ ልላክልህ ወይ?" ያለኝም አለ፡፡

እስካሁን ካርድ የላካቹልኝን ወዳጆች ስም አሁን አልዘረዝርም፣ ገና ነው::

ግና አላመሰግንም!

አንዳንዴ ምስጋና ወዳጅነትን፣ ቤተሰብነትን ያሳንሳል፡፡ ለትልቅ ደግነት ትንሽ ምስጋና አይመጥነውም፡ Good friends we have, Good friends we are!

ምናልባትም ደግነታችሁን አልረሳም!!!!!!ውለታንም አልረሳም!!! እላለው፤ እንዲህ ስል ደግሞ ከምሬን ነው…በግዜ ሂደት እናየዋለን፣አብረን ነንና፡፡

ሶስት ማስተሳሰቢያዎች፡

1. እንትና ይሄን ያህል የሞባይል ካርድ ሞላ ምናምን አልልም፤ ወይንም አሁን ላልኩት አላማ ለማዋሌም ማስረጃ አላቀርብም (ምናልባት ከደበረህ በፈለከው ግዜ የሞባይል ካርድህን ዋጋ ለመመለስ ዝግጁ ነኝ) መጨረሻ ላይ ግን የሰበሰብኩትን ብር መጠን እገልጻለው፡፡ ይህንን የአእምሮ እክል ያለበትን የኔ ቢጤ ለመርዳት የፈለገ ሰው ካለ ግን እስከ ሰኞ ድረስ መርዳት ይችላል፡፡

2. እዚሁ እኛ ውስጥ ለእንዲህ አይነት ተመሳሳይ አላማ (focused የሆነ ቢሆን አሪፍ ይመስለኛል፣ ባይሆንም ቅር አይለኝም) ሰው ለመርዳት የሚያስብ ወዳጅ ካለ እኔም በተራዬ የድርሻዬን ለመወጣት ከልብ ዝግጁ ነኝ፡፡

3. ይህንን የተቸገረን ሰው የሞባይል ካርድ እየላብር በማዋጣት መርዳት እንደባህል ብንወስደውስ?.. እና በየተወሰነ ግዜ ልማድ ብናደርገውስ? ነገረ አለሙ ለጨለመበት፣ ሰው የለኝም ለሚል አለንልህ ብንለውስ?

መልካም
ቀን 

https://www.facebook.com/eyob.mihreteab

No comments:

Post a Comment