Tuesday, September 12, 2017

“መሰንቆ እና ብትር” ከበዕውቀቱ ሥዩም

መሰንቆ እና ብትር (ወግ)

መሰንቆ እና ብትር
ከበዕውቀቱ ሥዩም
.
አያችሁት ብያ፣ የኛን እብድ፤
አምስት ጋሞች ይዞ፣ ጉራምባ ሲወርድ …”
አዝማሪ ጣፋጭ [1845 .]
.
የዳሞቱ መስፍን ደጃዝማች ጎሹ እና የቋራው ፋኖ ደጃዝማች ካሳ በኅዳር 19 1845 . ጉራምባ ላይ ጦርነት ገጠሙ። ካሳ፣ ከጥቂት ታማኝ ጭፍሮቻቸው ፊት ተሰልፈዋል። ጎሹም፣ በተለመደው የጀብድ መንገድ ከሰራዊታቸው ፊት ለፊት ቀድመው፣ ሲዋጉና ሲያዋጉ ውለዋል። ውጊያው እንደተፋፋመ፣ ደጃች ጎሹ በጥይት ተመትተው ወደቁ። የመሪውን መውደቅ እንደተረዳ የዳሞት ጦር ፀንቶ መመከት ተሳነው። ወዲያው የንቧይ ፒራሚድሆነ።ያለቀው አልቆቀሪው ተማረከ። 
ከምርኮኞች አንዱ፣ አዝማሪው ጣፋጭ ነበር። ጣፋጭ፣ የደጃች ጎሹ አዝማሪ ስለነበር በብዙ ጦር ሜዳ ላይ ውሏል። በጌታው ጠላት እጅ ሲወድቅም የመጀመሪያው አይደለም። በራስ ይማም ዘመንም እንዲሁ፣ ደጃዝማች ማጠንቱ የተባለ መስፍን ደጃዝማች ጎሹን ድል በነሳ ጊዜ፣ ከጌታው ጋር ተማርኮ ነበር።
ይሁን እንጂ ያኔ ዝንቡን እሽ ያለው አልነበረም። ጣፋጭ፣ የደጃች ማጠንቱ ምርኮኛ ቢሆንም፣ የእግር ብረት አልገባበትም። እንዲያውም፣ በድል አድራጊው አዳራሽ ውስጥ ያሻውን ከማንጎራጎር አልተከለከለም ነበር። በወቅቱም፣ አዝማሪው ጣፋጭ ይህንን ገላጋይ ዝማሬ አቅርቦ ነበር፤
አስረህ አንድ አትግደል፣ ደጃዝማች ማጠንቱ 
ለጀብዱ እንደሆነ፣ ይበቃል ስምንቱ።
ጣፋጭ፣ ደጃዝማች ማጠንቱ በጦር ሜዳ ላይ ስምንት ወታደር መግደሉን አስታውሶ፣ አሁን ተማራኪውን ቢገድል የሚጨመርለት ክብር እንደሌለ አስታወሰው። በሁለት መስመር ግጥም ለድል አድራጊው የሚገባውን መወድስ ሳይነፍግ፣ የጌታውን ሕይወት ለመታደግ ጥሯል። ድል አድራጊው ደጃች ማጠንቱም ጎሹን ሳይገድለው ቀረ።
በዚህ በኅዳር ዕለት ጦርነት ግን፣ አዝማሪው ጣፋጭ በቋረኛው ካሳ ጦር ተማርኳል። ተስፋና ፍርሀት ከፊቱ ተደቅነዋል። ባንድ በኩል፣ አዝማሪን መግደል ነውር የሚያደርገው ባህል ጋሻ ሁኖት ከክፉ እንደሚታደገው ተስፋ ያደርጋል። በሌላ በኩል፣ ደጃዝማች ካሳ ይህን ደምብ ለማክበራቸው ርግጠኛ አይደለም።
እነሆ፣ አዝማሪው በካሳና በጭፍሮቻቸው ፊት ቆሟል። ቀጥሎ ምን እንደተከሰተ የሚተርኩልን ለዘመኑ ቅርብ የነበሩት አለቃ ወልደማርያም ናቸው፤
አዝማሪ ጣፋጭተይዞ በቀረበ ጊዜ ባደባባይ አቁመው ደጃች ካሳእንዴት ብለህ ሰደብኸኝቢሉት እጅግ ተጨነቀ፤ እንዴህም አለ፤
እወይ ያምላክ ቁጣ እወይ የግዜር ቁጣ
አፍ ወዳጁን ያማል ሥራ ሲያጣ።
እንዲህም ቢል ሞት አልቀረለትም፤ በሽመል ገደሉት።
አለቃ ተክለየሱስ ዋቅጅራ ከሁለት ትውልድ በኋላ በጣፉት የጎጃም ታሪክ ውስጥ ደግሞ የሚከተለውን ተጨማሪ መስመር እናገኛለን፤
አወይ ያምላክ ቁጣ አወይ የግዜር ቁጣ
አፍ ወዳጁን ያማል ሥራ ሲያጣ
ብትር ይገባዋል ያዝማሪ ቀልባጣ
ከመቶ አመት በኋላ ታዋቂው ዘመናይ የታሪክ ጸሐፊ ተክለጻድቅ መኩሪያ በጻፉት ጥናትምብትርየሚለውንሽመልበሚል ቃል ከመተካት በስተቀር ያለቃ ተክለየሱስን ቅጂ ማስተጋባት መርጠዋል፣
እወይ ያምላክ ቁጣ …
ሽመል ይገባዋል ያዝማሪ ቀልባጣ።
.
ጣፋጭ፣ የደጃች ካሳን ምሕረት አጥብቆ የሚፈልግ ምርኮኛ ሆኖ ሳለ፣ እንዴት ተሽቀዳድሞ በራሱ ይፈርዳል? እንዴት ሽመል/ብትር ይገባዋል ያዝማሪ ቀልባጣ ብሎስ ራሱን ለቅጥቀጣ ያቀርባል?
የጣፋጭን ፍርድ በመመዝገብ ቀዳሚ የሆኑት አለቃ ወልደማርያም ታሪክ ውስጥ መደምደሚያው ስንኝ አለመጠቀሱ አንድ ነገር የሚጠቁም ይመስለኛል። ስንኙ ምናልባት ከጊዜ በኋላ የተጨመረ ይሆናል።
የኔ ግምት እንዲህ ነውአዝማሪ ጣፋጭ በደጃዝማች ካሳና አጃቢዎቻቸው ፊት ይቀርባል፤
ደጃች ካሳ   እንዴት ብለህ ሰደብኸኝ?
ጣፋጭ፣ በጦርነቱ ዋዜማ በደጃች ካሳ ላይ ያወረደውን ዘለፋ እዚህ ቢደግም፣ የድል አድራጊውን ቁጣ ከማቀጣጠል ውጭ የሚፈይድለት ነገር የለም። ስለዚህ የመጨረሻ መሳሪያውን ለመጠቀም ወሰነ። ቧልት! …. ካሳና ጣፋጭ በጎሹ ቤት በሎሌነት ሲኖሩ፣ ካሳ ቀልድና ፈሊጥ እንደሚወድ ያውቃል። ጣፋጭ መሰንቆውን ቃኝቶ ይህን በግለ ሂስ የተሞላ የቧልት ዘፈን ዘፈነ፤
ጣፋጭ   ህምም
እወይ ያምላክ ቁጣ እወይ የግዜር ቁጣ
አፍ ወዳጁን ያማል ሥራ ሲያጣ።
ካሳ አልሳቀም። አዝማሪው የከፈተውን ተውኔት እንዴት መቀጠል እንዳለበት እያሰበ ይሆናል። ደጃዝማች ካሳ፣ ራሱን የመለኮት ተውኔት ፍሬ አድርጎ ስለሚቆጥር ፍርዱን ሳይቀር ተውኔታዊ ማድረግ ይወድ ነበር። የራስ አሊን እናት በማረከም ጊዜገረድ ትሰለጥናለች እመቤት ትፈጫለችየሚለውን የፍካሬ ኢየሱስ ትንቢት ለማስፈጸም ወይዘሮ መነን ባቄላ እንድትፈጭ ፈርዶባት ነበር።የኮሶ ሻጭ ልጅብሎ የሰደበው ቀኛዝማች ወንድይራድን ደግሞእናቴ ከገበያ ሳይሸጥላት የቀረ ኮሶ ስላለ እሱን ተጋበዝብሎ፣ ከመጠን ያለፈ ኮሶ አስግቶ ለመቅጣት የሆነ የተውኔት ስጦታ ያስፈልጋል። ያገራችን ጸሐፌ ተውኔቶች በፍቅሩ የነሆለሉት ብጤያቸው ስለሆነ መሆን አለበት።
ደጃች ካሳ   (ወደ አጃቢዎቹ ዞሮ)
ብትር ይገባዋል ያዝማሪ ቀልባጣ።
.
ጣፋጭ በቧልት የጀመረውንካሳ በትራጀዲ ደመደመው።
.
* * *
ጣፋጭን ለድብደባ የዳረገው ዝማሬ ግጥም ይሄ ነበር
አያችሁት ብያ፥ የኛን እብድ 
አምስት ጋሞች ይዞ፥ ጉራምባ ሲወርድ
ያንጓብባል እንጂ፥ መች ይዋጋል ካሳ
ወርደህ ጥመድበት፥ በሽንብራው ማሳ
ወዶ ወዶ 
በሴቶቹ  በነ ጉንጭት ለምዶ።
* * *
.
አያችሁት ብያ የኛን እብድ” [መስመር ]
ብያ ዛሬ ለመረሳት ከደረሱት ያማርኛ ጥንታዊ ቃላት አንዱ ሲሆንእኮ፣ አይደልማለት ነበር።አያችሁት ብያሲልም “አይታችሁታል አይደል?” ማለት ነው። ቴዎድሮስ መቅደላ ላይ ራሱን ገድሎ በወደቀ ማግስት ከወረዱ የሙሾ ግጥሞች አንዱ፣ አያችሁት ብያ ያንበሳውን ሞት የሚል ስንኝ አለው። ይህም በጊዜው ቃሉ የተለመደ እንደነበር ያመለክታል።
እብድ ተብሎ ካሳ በይፋ ሲጠራ ለመጀመሪያ ጊዜ በታሪክ የምንሰማው ከአዝማሪ ጣፋጭ ሳይሆን አይቀርም። ጣፋጭ ይህን ሲል፤ የጊዜውን አስተያየት እያስተጋባ ነው? ወይስ በራሱ ምርመራ የደረሰበት ነበር? አላውቅም። አለቃ ተክለየሱስ ከግማሽ መቶ አመት በኋላ በጐንደር ሲወርድ የነበረውን ግፍ ዘግቦ፣ የሕዝቡን ምላሽ ምን እንደነበር ሲጽፍ፣ከዚህ በኋላ፣ የበጌምድር ሰውይህስ የደህንነትም አይደለእያለ አመል አወጣንጉሡንም ጠላው። ሌሊት በተራራ እየቆመ፣ እንደ ሳሚ ወልደ ጌራእብዱ ገብረኪዳንእያለ ተሳደበይላል። (“ገብረኪዳንየአፄ ቴዎድሮስ የክርስትና ስም እንደነበረ ባልታወቀ ደራሲ ተጽፎ Fusella ባሳተመው ዜና መዋዕል ተጠቅሷል።)
.
አምስት ጋሞች ይዞ፣ ጉራምባ ሲወርድ [መስመር ]
ጋሞችየሚላቸው ባለ አፍላ እድሜ ላይ ያሉትን ጋሜዎች ነው። ባዝማሪው አይን ሲመዘኑ የደጃዝማች ካሳ አጃቢዎች እድሜያቸው ለጋ፣ ቁጥራቸውም ጥቂት ነው። በርግጥም የካሳ ጭፍሮች ማነስ ለባላጋራዎች ግራ የሚያጋባ ነበር። ባነጋገር ፈሊጣቸው የታወቁት ራስ አሊ የቋራው ካሳን ሰራዊት ከሩቅ አይተው ከገመቱት በታች ቢሆንባቸው፣ጦረኛ እንዳንለው አነሰ፤ ሰርገኛ እንዳንለው በዛብለው ነበር።
ጉራምባ” (ጉር አምባ) በዛሬው የደንቢያ ወረዳ፣ ጎርጎራ በተባለው ንኡስ ወረዳ ውስጥ የሚገኝ ስፍራ ነው። ደጃዝማች ካሳ ይህን ስፍራ የመረጡት ለመከታ የሚያመች አምባ ሆኖ ስላገኙት ሳይሆን አይቀርም። አዝማሪው ጣፋጭ በግጥሙ ውስጥጉር አምባየሚለውን ነባር ስምጉራምባብሎ አሸጋሽጎታል። ይህን ያደረገው ስፍራውንጉራ መንፊያብሎ ለመተርጎም እንዲያመቸው ይመስላል። ጣፋጭም የቋራው ካሳን ለይስሙላ እንጂ የምር መዋጋት የማይሆንለት ጦረኛ አድርጎ ይገምተው እንደነበር ቀጣዩ መስመር ያሳያል።
.
ያንጓብባል እንጂ መች ይዋጋል ካሳ” [መስመር ]
ያንጓብባልየሚለው ቃልአጊጦ በመልበስ ቄንጥ ባለው አካሄድ ይሄዳል፣ ዳር ዳር ይላልማለት ነው። ቃሉን የሚከተለው ከአለቃ ዘነብመጽሐፈ ጨዋታየተቀነጨበ አንቀጽ የበለጠ ያብራራዋል፣
ሰማይ ከዚያ ላይ ሆኖ አንጓቦብን የሚኖር ከቶ ምንድር ነው? ቀን ፀሐይን ሌሊት ጨረቃንና ከዋክብትን ተሸልሞ ዘወትር እኔን እኔን እዩኝ እዩኝ እያለ ያደክመናልእንደዚህ የኮራ እንደ ሰም ለመቅለጥ ነው እንጂ ፊቱን እንዴት ያየው ይሆን? ኩራቱም ምድር አስለቅቆታል። ምን ይሆናል እንደሚያልፍ አያውቅምን?”   [ክፍል 15 አንቀጽ 16]
ይህ ዳር ዳር ማለት የቋራው ካሳ ጠላቶቹን የሚያዘናጋበት ልዩ የጦር ስልት ነበር። በጠላቶቹ አይን ግን እንደ ፍርሀት ይቆጠር ነበር። ለአብነት ያክል፣ አለቃ ወልደማርያም በደጃች ካሳና በራስ አሊ መሐል የተደረገውን ውጊያ አስመልክተው ሲጽፉ፤ “ራስ አሊ አይሻል በሚባል ሜዳ ጦርዎን ሰርተው ተቀምጠው ሳሉ ደጃች ካሳም ዳር ዳሩን ይዞሩ ጀመሩ። ሰውም የፍርሀት መስሎትተመልሶ ሊሄድ ነውይል ጀመረ።
መች ይዋጋልየቋራው ካሳ ደፋርና ጽኑ ተዋጊ ቢሆንም ጉልበቱን መዝኖ መሸሽም ያውቅ ነበር። ደጃዝማች ጎሹ 1840 . ለፈረንሳዊው ሚካኤል አባዲ በጻፉት ደብዳቤተካሳ ጋራ የተዋጋነ እንደሆነ ጎንደር እገባለሁ እንገናኛለን፤ ወደ ቆላ የሸሸ እንደሆነ …” ያሉት ይህን ስለሚያውቁ ይመስላል። እንደገመቱት፣ ካሳ ወደ ትውልድ ቦታው አፈግፍጎ ከርሟል። አዝማሪው ጣፋጭ “… መች ይዋጋል ካሳያለው ይህን ሁኔታ በማጤን መሆን አለበት። ይሁን እንጂ፣ ካሳ ለጣፋጭ ያልተገለጠለት ጠንካራ ጎን ነበረው። ጠላቶቹ ሽሽቷል ብለው ሲዘናጉ እንደገና አፈር ልሶ ተነስቶ ማጥቃትና ማሸነፍ ይችል ነበር።
.
ወርደህ ጥመድበት በሽንብራው ማሳ“ [መስመር ]
ወርደህየሚለውን ቃል አዝማሪው በዚህ ዝማሬ ውስጥ ሁለቴ ተጠቅሞበታል። መስመር 2 ላይጉራምባ ሲወርድብሎ ካሳን የገለጠውን ያክልወርድህ ጥመድበትብሎ ጎሹን ይጎተጉተዋል። የመፋለሚያውን ቦታ ቆላነት ያሳስባል፤ ወደ ቆላ ወረደ ይባላልና።ጥመድበአማርኛ ብዙ ትርጉም አለው፤ ከግጥሙ ዐውድ ጋር የሚሄደውአሽክላን ዘረጋ፣ ወይም የጠፋ ሰውን አጥምዶ ሸምቆ ለመያዝ በጎደጎደ አደባየሚለውን ነው። ስለማይዋጋ ካሳን አድብቶ መያዝ እንደሚያዋጣ ጣፋጭ ሀሳብ እያቀረበ ነው።
በሽንብራው ማሳሲል አዝማሪ ጣፋጭ ስለየትኛው ነው የሚያወራው? “ካሳከሚለው ቃል ጋር እንዲገጥመለት ይሆን? የለም፤ እኔ እንደሚመስለኝ ቃሉ ታስቦበት የተመረጠ ነው። ደጃች ጎሹ የቋራውን ደጃች ካሳ አባርረው ደንቢያን በጃቸው ባስገቡበት ዘመን ከምግብ ሁሉ የሚወደውን የሽንብራ አዝመራ አውድመውበታል ይባላል። ጣፋጭወርደህ ጥመድበት በሽንብራው ማሳያለው ያንን አስታውሶ ይመስለኛል። አለቃ ዘነብ፣ያን ጊዜም ቋራ ሁሉ ጠፍ ሆኖ ነበር። ልጅ ካሳም ለባላገሩ ሁሉ ብዙ ብር ሰጡት። መቆፈርያ ግዛ ብለውከወታደሩ ጋር ብዙም ቆፍረው ዘሩያሉት የሚታወስ ነው።
.
ወዶ ወዶ!” [መስመር ]
ወዶ ወዶጣፋጭ ይህን የተጠቀመው ለማሽሟጠጥ ነው፤ወድያ ወድያእንደማለት ነው። በዛሬ አማርኛ ብንመልሰውድንቄም ድንቄምእንል ነበር።
.
በሴቶቹ በነ ጉንጭት ለምዶ” [መስመር ]
ጉንጭትለጉንጫም ሴት የሚሰጥ ቅጥል ነው። ጣፋጭበነ ጉንጭትሲል ደጃዝማች ካሳን በዘመኑ ያጅቡ ከነበሩት ቅሬዎች (ጋለሞቶች) አንዷን ጉንጫም አስታውሶ ይሆን?  “በነ ጉንጭት ለምዶ …” ካሳ ከሴቶቹ ከነጉንጭት የለመደው ምንድነው? በጣፋጭ እይታ መሽቀርቀር፣ የእዩኝ እዩኝ ማለትን ተግባሮች ሁሉ ድምር የሆነውማንጓበብመሆኑ ነው።
ጣፋጭም ሆነ ካሳ፣ ወንድን እንደ መለኮት ከፍ ከፍ የሚያደርግ፣ ሴትን እንደ ጉድፍ የሚያጣጥል ማኅበረሰብና ዘመን ፍሬዎች ናቸው። በዚህ አይነቱ ዘመን አንድ ጦረኛ ጀብዱው ከከተሜ ቅሬዎች ተግባር ጋር መነጻጸሩን ሲሰማ ደም ብቻ እንደሚያጸዳው ውርደት አድርጎ ቢቆጥረው አይገርምም።
የጣፋጭን ፍጻሜ የወሰነችውም ይቺ የመጨረሻዋ መስመር ሳትሆን አትቀርም።
.
አዝማሪ ጣፋጭ (1790ዎቹ-1845 .)
እና ድርሰቶቹ
*
እወይ ያምላክ ቁጣ፣ እወይ የግዜር ቁጣ፤
አፍ ወዳጁን ያማል፣ ሥራ ሲያጣ።
[ኅዳር 19 1845 .ጉራምባ]
.
* *
ክፉ የክፉለት፣ ይሆን የነበረ፤
ብሩንይሙትብሎ፣ አለ የመከረ።
[ኅዳር 19 1845 .ጉራምባ]
.
* * *
አያችሁት ብያ፣ የኛን እብድ፤  
አምስት ጋሞች ይዞ፣ ጉራምባ ሲወርድ፤
ያንጓብባል እንጂ፣ መች ይዋጋል ካሳ፤
ወርደህ ጥመድበት፣ በሽንብራው ማሳ፤
ወዶ ወዶ 
በሴቶቹ  በነ ጉንጭት ለምዶ፤
(ሐሩ ቋዱ፣ ለውዙ ገውዙ አለ ቋራ፤
መንገዱ ቢጠፋ፣ እኔ ልምራ።)”
[ኅዳር 19 1845 .ጉራምባ]
.
* * * *
አስረህ አንድ አትግደል፣ ደጃዝማች ማጠንቱ፤ 
ለጀብዱ እንደሆነ፣ ይበቃል ስምንቱ።
[1820 .ቋሚ ጨርቅ]
.
በዕውቀቱ ሥዩም

ሰኔ 2009 .

No comments:

Post a Comment