Monday, May 9, 2016

“የሌላውን አስመስሎ የዘፈነን አላደንቀውም”

Written by  ናፍቆት ዮሴፍ
ድምፃዊው 150ሺ ብር ለበጐ አድራጐት ድርጅት ለገሰ

የትዝታው ንጉስ በሚል የሚታወቀው አንጋፋው ድምፃዊ (ዶ/ር) አርቲስት ማህሙድ አህመድ ባለፈው ሳምንት በማሪዮት ኢንተርናሽናል ሆቴልና በያሬድ ሙዚቃ ት/ቤት በተለያዩ
ዝግጅቶች የ75ኛ ዓመት የልደት በዓሉን አክብሯል፡፡ የልደት በዓሉን ምክንያት በማድረግም ከልጅነት እስከ እውቀት ከተነሳቸው በርካታ ፎቶግራፎች መካከል 75 ያህሉ ተመርጠው
ለእይታ ቀርበውለታል፡፡ የፎቶ ኤግዚቢሽኑ በተከፈተበት ወቅት ባደረገው ንግግርም፤ “ብዙ የሙያ ጓደኞቼን በሞት አጥቻለሁ፤ እኔ እስካሁን በጤናና በሰላም እዚህ በመድረሴ
እግዚያብሔርን አመሰግናለሁ” ሲል የለቅሶ ሳግ ንግግሩን አቋርጦታል፡፡ አርቲስቱ ባለፈው እሁድ “ሲንደርታ ዴቨሎፕመንት ኢትዮጵያ” በተሰኘ የበጐ አድራጐት ድርጅት ውስጥ
በመገኘት ከ45 ወላጅ ያጡ ህፃናት ጋር የፋሲካን በዓል ሲያጫውታቸውና ሲዘፍንላቸው ያሳለፈ ሲሆን ውሎ ምሳ አብሯቸው ከተመገበ በኋላ ለድርጅቱ 150ሺህ ብር ለግሶ
አምባሳደራቸው እንደሚሆን ቃል ገብቶላቸዋል፡፡ በፎቶ ኤግዚቢሽኑ መክፈቻ ላይ የተገኘችው የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ ከአንጋፋው ድምፃዊ ማህሙድ አህመድ ጋር
አጭር ቃለምልልስ አድርጋለች፡፡ እነሆ፡-


75 ዓመታት በህይወት መቆየት… ሶስት መንግስታትን ማየት… በሙያ ለረጅም ጊዜ በሰው ተወድዶ መቆየት ምን ስሜት ይሰጣል?
እ…ም…ምን ስሜት ይሰጣል ነው ያልሺኝ? ከባድ ጥያቄ ነው፡፡ ስሜት እንደ ምግብ… እንደ መጠጥ ጣዕሙ በቃላት የሚገለፅ ባለመሆኑ ጥያቄው ከባድ ነው፡፡ የሆነ ሆኖ የማልዋሺሽ በጣም ደስታ ይሰማኛል፡፡እግዚአብሔር ዕድሜና ጤና ሰጥቶ ለዚህ ስላበቃኝ ደስተኛ ነኝ፡፡ 
እስካሁን በጤናህ ላይ ያጋጠመህ ችግር የለም? እድሜን ተከትለው የሚመጡ የጤና ችግሮች ይኖራሉ ብዬ ነው?
እግዚአብሔር ይመስገን እስካሁን ምንም የጤና እክል አላጋጠመኝም፤ ከዚህ በኋላ ቢያመኝም እችለዋለሁ፡፡ እንዳልሽው የሰው ልጅ እድሜው ሲገፋ የማያመው ነገር የለም፤ ከእነምሳሌው  አባቶች፣ “እርጅና ብቻህን ና” ይላሉ፡፡ እርጅና ብቻውን አይመጣም፤ ብዙ ጓዝ ያስከትላል፡፡ ቢሆንም እኔ እስካሁን ጤነኛ ነኝ፤ ከዚህ በኋላ የሚመጣውን ነገር አላውቅም፡፡ 
ለልደትህ የዛሬ ሳምንት ከአሜሪካ መምጣትህን ሰምቻለሁ፡፡ ኑሮህ ጠቅላላውን አሜሪካ ሆኗል ማለት ነው?
ኑሮዬን ጠቅልዬ አሜሪካ አላደረግሁም፡፡ እዚያ የምሄደው ለስራ ነው፡፡ እዚያ የሚያሰሩኝ ሰዎች ረጅም ቀጠሮ እየያዙ ነው የሚወስዱኝ፡፡ የተለያዩ ኮንሰርቶች እየሰራሁ ስራዬ ሲያልቅ ወደ አገሬ እመለሳለሁ፡፡ ከዛም ወደ ኢትዮጵያ ስመጣ በቀጠሮ ነው፡፡ አሁንም ለዚህ የልደት በዓል በ “አሻራ ፊልምስ” ሃላፊዎች ቀጠሮ ተይዞልኝ ነው የመጣሁት፡፡ 
ከድምፃዊ ጐሳዬ ተስፋዬ ጋር “አይባባም ሆዴ” የተሰኘ ተተኪ ማፍራትህን የሚገልጽ ነጠላ ዘፈን አውጥታችኋል፡፡ በእርግጥ ተተኪ አፍርቼአለሁ ብለህ ታስባለህ?
ማፍራቴን እርግጠኛ ነኝ፤ እንደውም ከሚጠበቀው በላይ ተተኪዎች አሉ፡፡
በምሳሌነት የምትጠቅስልኝ ይኖራሉ?
በድምፅ፣ በግጥም፣ በዜማና በአጠቃላይ ሁኔታዎች የተሻለ ነገር እየመጣ እንጂ ወደ ኋላ አልተጐተተም፡፡ ይህን ያህል ነው ብዬ ልናገረው በማልችለው ሁኔታ በቂ ተተኪ አለ፡፡ አዲሱ ትውልድ በጣም ፈጣንና ጥሩ ጥሩ የሙዚቃ ስራ እየሰራ ነው፡፡ እድገታችሁን በኔ መጠን አድርጉ ማለት አልችልም፤ ከኔ የተሻለ ይሰራሉና፡፡ አሁን ጊዜው ሙዚቃን የተሻለ አድርጐ ለመስራት አመቺ ነው፡፡ 
የአንተን ድምጽ በማስመሰል የሚዘፍኑ ወጣቶች አሉ፡፡ የተደነቅህባቸውና ያስደመሙህ ድምፃውያን አሉ?
በመጀመሪያ እኔ እኔ ነኝ፤ ማንም የእኔን አስመስሎ ሊጫወት አይችልም፡፡ ምክንያቱም መቶ በመቶ አስመስሎ መዝፈን ቀላል አይደለም፡፡ ደግሞ ቢያስመስልም አላደንቀውም፡፡ 
ለምን?
በቃ አላደንቀውም፡፡ ያ ወጣት ራሱን ማውጣት ነው ያለበት፡፡ አንድ ዘፋኝ የሌላውን አስመስሎ ሲዘፍን አላጨበጭብለትም፡፡ የእከሌን ዘፈን የሚጫወተው፣ ያ የማህሙድን ድምጽ የሚያስመስለው፣ ያ የጥላሁንን ዘፈን የሚዘፍነው እየተባለ ጣት መጠቋቆሚያ እንዲሆን አልፈልግም፡፡ ይሄ ሰው ራሱን መፍጠርና ከሌላ ሰው ድምጽ ተፅዕኖ መውጣት አለበት፡፡ እንዲህ አይነቱን ዘፋኝ ባደንቀው ምንም ስለማላመጣ ከማደንቀው ብመክረው ይሻለኛል፡፡ ምክር ብዙ ውጤት ያመጣል፡፡ 
ግን እኮ አንዳንድ ድምፃዊያን እነሱን አስመስለው ለሚዘፍኑ ወጣቶች ሽልማት እስከ መሸለም ሁሉ ይደርሳሉ?
እኔ ሌላውን ወክዬ መናገር አልችልም፤ ያ የእነሱ ስሜትና ፍላጐት ነው፡፡ የእኔን ተናግሬያለሁ፤ እንኳን መሸለም አይደለም አድናቆት አልቸርም፡፡ ጥሩ የሚሆነው ማስመሰልን ማበረታታት ይሁን ራሱን ፈልጐ እንዲያገኝ መርዳት ሁሉም የራሱን ፍርድ የሚሰጥበት ይሆናል፡፡ 
ወደፊት ከአንተ ምን አዲስ ነገር እንጠብቅ? ምን ለመስራት አስበሀል?
በቅርቡ አዲስ ነገር ብትጠብቁ ደስ ይለኛል፡፡ ምክንያቱም አዲስ ዘፈን ሰርቼ ጨርሻለሁ፡፡ 
በቅርቡ ማለት መቼ ነው?
በዚህ ቀን ነው ለማለት አልችልም፡፡ ያ ጊዜ ለእኔም ይደንቀኛል፡፡ እግዚአብሄር ያለ ቀን ብቅ ይላል፡፡ ዋናው አዳዲስ ዘፈኖች ተሰርተው መጠናቀቃቸውን አድናቂዎቼ እንዲያውቁ እፈልጋለሁ፡፡ 
የ “አሻራ ፊልምስ” ባለቤቶች በህይወት እያለህ ልደትህን ለማክበር ሲታትሩ ምን ተሰማህ?
እውነት ለመናገር በጣም ነው ደስ ያለኝ፡፡ በደስታ ነው ጥያቄያቸውን የተቀበልኩት፡፡ እነሱ እኔን ለማክበርና ልደቴን ለማሰብ ደፋ ቀና ሲሉ፣ እኔ እንዴት በደስታ አልቀበልም?! በዚህ አጋጣሚ የ“አሻራ ፊልምስ” ዳይሬክተርና ፕሮዲዩሰርን ታጠቅ ተ/ማሪያምንና የስራ ባልደረቦቹን በጣም አመሰግናለሁ፡፡ 
ዝግጅታቸውን እንዴት አገኘኸው? 
በጣም ጥሩ አድርገው ነው ያዘጋጁት፤ በጣም ደስ ብሎኛል፡፡
ልደትህን አስመልክቶ በቀረበው የፎቶ ኤግዚቢሽን ላይ 75 ፎቶዎች ለእይታ ቀርበዋል፡፡  እንደው በአጠቃላይ ምን ያህል ፎቶዎች አሉ? 
ከ200 በላይ የተዘጋጁ ፎቶዎች ይኖራሉ፤ ይህ የእኔ ግምት ነው፡፡ ለስራ በየሀገሩ ስሄድ የተነሳኋቸው ፎቶዎች አልቀረቡም፡፡ በርካታ ፎቶዎች ናቸው ያሉኝ፡፡ 
በህይወትህ ይህን ሳላደርግ ቀርቻለሁ ብለህ የሚቆጭህ ነገር አለ?
በፍፁም!! እኔ ከጫማ ጠራጊነት ተነስቼ ወደ ዕውቅና ደረጃ የደረስኩ ሰው ነኝ፡፡ ተወዳጅነትና የሰው ፍቅር ተቀዳጅቻለሁ፡፡ በጣም ብዙ ነገር ያየሁና እግዚአብሔርን የማመሰግን ሰው ነኝ፤ ምንም የሚቆጨኝ ነገር የለም፡፡ በሰው ተወዶ በሰው ተከብሮ፣ ጤናና እድሜ አግኝቶ መኖር ትልቅ ፀጋ ነው፡፡ 
ከዚህ በኋላ ምን ያህል እድሜ ብትቆይ ደስ ይልሃል?
ወቸ ጉድ! ደግሞ በፈጣሪ ስራ ልግባ፣ ስንት አመት መኖር ትፈልጋለህ ትያለሽ? እሱ እንደፈቀደ ነዋ! ፈጣሪ እንደወደደ፡፡ እስከ ዛሬስ ይህን ያህል እድሜ የሰጠኝ አምላክ አይደለም እንዴ?! የኔ ታላቆችም ታናሾችም የነበሩ ብዙ ጓደኞቼ እኮ አልፈዋል፡፡ ይህ የእግዚአብሔር ስራ ነው፡፡ ስለዚህ እሱ የፈለገውን የወደደውን ያህል እድሜ ይስጠኝ፤ አለቀ፡፡
http://www.addisadmassnews.com/

Monday, December 21, 2015

“በወሮበሎች ስውር ደባ” ተሰቃይቻለሁ (ከአዲስ አድማስ)

- በየሄድኩበት ሁሉ ጥቁር ካልሲ ይጥሉብኝ ነበር
- “መድሃኒት እየሰረቀ ይሸጣል” ብለው አስወርተውብኛል

አዲስ አበባ ነው ተወልደው ያደጉት፡፡ የዕድሜያቸውን ግማሽ ያሳለፉት በውጭ አገራት ነው፡፡ በማህበረሰብ ጤና የማስተርስ ዲግሪ
ይዘው ለንደን በሚገኝ አንድ ትልቅ ሆስፒታል ውስጥ በሲኒየር ነርስነት እያገለገሉ እንደሚገኙ ይናገራሉ፡፡ አቶ ሄኖክ አያሌው ላለፉት
አራት ዓመታት “በወሮበሎች ስውር ደባ” (Gang stocking) ሲሰቃዩ እንደቆዩና በተለያዩ የራሳቸው ጥረቶች ከችግሩ ነፃ መውጣታቸውን
ይገልፃሉ፡፡ የወሮበሎች ደባ፤ አንድ ግለሰብ በወሮበሎቹ ስሙ ከጠቆረና “ብላክ ሊስት” ውስጥ ከገባ በኋላ ወደ ውድመት እንዲያመራ
የሚያደርግ ስርዓት ነው ይላሉ አቶ ሄኖክ፡፡













በወሮበሎቹ ወጥመድ ውስጥ የገባሁት በእንግሊዝ አገር ሳለሁ በተዋወቅኋት ዮዲት ጉዲት የተባለች ሴት ሰበብ ነው የሚሉት የታሪኩ
ባለቤት፤ ከእሷ ጋር ባለመግባባት ከተለያዩ በኋላ በወሮበሎቹ ጥቃት መከራቸውን ማየታቸውን ያስረዳሉ፡፡ “የወንበዴዎቹ ዓላማ
ያጠመዱትን ሰው ስም በማጥፋትና በማጠልሸት በብቸኝነት፣ በጭንቀትና በፍርሃት ማሸበር ነው ይላሉ አቶ ሄኖክ፡፡ በተከበርኩበት
ትልቅ ሆስፒታል ውስጥ “መድኃኒት እየሰረቀ ይሸጣል” ብለው አስወርተውብኛል ያሉት የታሪኩ ባለቤት፤ በየሄድኩበት ሁሉ ጥቁር ካልሲ
ይጥሉብኝ ነበር… በማለት የደረሰባቸውን ያስረዳሉ፡፡ ባለፈው አራት ዓመት የደረሰባቸውን ስቃይም፣ “የዲያስፖራው ስውር ደባ” በተሰኘ
መፅሃፋቸው ተርከውታል፡፡ መፅሀፉ “The Jaws of Evil” በሚልም ወደ እንግሊዝኛ ተተርጉሞ ባለፈው ሳምንት ከአማርኛው ጋር
ተመርቋል፡፡ የ49 ዓመቱ ጐልማሳ አቶ ሄኖክ አያሌው “የወሮበሎች ስውር ደባ” በሚሉት ጉዳይ ዙሪያ ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት
ዮሴፍ ጋር ተከታዩን ሰፊ ቃለ-ምልልስ አድርገዋል፡፡

Monday, November 16, 2015

’’ዜጎቿን ለማስራብ እየተጋች ያለች ሀገር ኢትዮጵያ !’’


ሰለሞን ዮሃንስ
እኔ ርሀብን የማውቀው ለሰዓታት ነው:: ለዚያውም ምን ያህል ሰዓት እህል ሳልቀምስ መቆየት እችላለሁ ብዬ የሞከርኳት የቅብጠት ቆይታ ፡፡ያጥወለመለኝን ፤ማይትያቃተኝን ፤ያዘፈዘፈኝን ፍጹም ያዛለኝን የያኔው ርሃቤ ከዛሬው ርሃብ ውሎ ካደረበትና የሚላስና የሚቀመሰውን ካየ ቀናት የተቆጠሩበት ወገኔ ጋር ፈጽሞ ለንጽጽር የሚቀርብ አይደለም፡፡ እኔስ ያኔ ያገኘሁትን አግበስብሼ ነፍሴ መለስአለች ፡፡
ዛሬስ ወገኔማ ማሳው ደርቆ ፤ጎተራው ባዶ ሆኖ ተስፋ በሌለው ውል የመጨረሻ ቀኑን ይቆጥራል፡፡
ርሃብ ስንት ቀን ይፈጃል? ብዬ ልፈላሰፍ አይዳዳኝም፤ ወገኔ የሚላስ የሚቀመስ አጥቶ አጥንቱ እተቆጠረ አይኑ እየፈጠጠ ሰውነቱ ተስለምሞልሞ መጨረሻውን ይጠብቃል  …እንስሳቱማ መንገዱን ጠርገውለታል ፡፡
ለዚህ ደግና ኩሩ አፈርገፊ ህዝብ ይህ አይገባውም ነበር ፡፡
ይህ ደግ ህዝብ የሚቀጣው ለምን ይሆን ???
ዛሬም የዩቱ የሙዚቃ ባንድ   አባለቱንቱን ወዴት ናችሁ  ? ቦብ ጌልዶፍስ ምነው ዝም አልክ ? ማይክል ጃክሰን  ሆይ መቃብሩን ፈንቅልና ከሙያ አጋሮችህ ጋር ድረስልን እንበለው?
ምን አይነት ጉድ ነው የተጠናወተን ?
ማነው እንባውን እያዘራ ኢትዮጵያን ርሃብና ርዛት ከምድርሽ አይጥፋ ብሎ አምርሮ የረገማት?
ምን አይነት ክፉ ቀን ነው ተጣብቶ አለቅ ያለን ?
ይሄ ሀገሩን የሚመግበው ገበሬ የማይደክመው ፍጡር ዛሬ ተረታሁ ብሎ ይጣራል የሰሚ ያለህ እያለነው ፡፡ ጎታው ባዶ ሆኖ መሬቱ ደርቆ የሚውዳቸው እንስሳቱ ሞተውበት ድፍርስ እንባውን እያነባ ባዶ ማረሻ ይዞ ተስፋው ተሟጦ የሚመጣውን ይጠባበቃል፡፡
ያች ምስኪን እናት የልጆቿ የርሃብ እሪታ ጸንቶባት ሰቆቃ መስማት ተስኗት ከልጆቼ በፊት እኔን አስቀድመኝ ብላ ፈጣሪዋን ብትማጸንም  ልጆቿን በሞት መነጠቅ አልቀረላትም፡፡
እሷም የታጠፈ አንጀትዋን መቀነት አድርጋ እንባዋን ታዘራለች፡፡
እኛስ ?
እኛ ደግሞ እዚህ በስሜታዊነት ብቻ ማዶለማዶ ሆነን በቃላትና ቁጥርን መባስተባበል ተጠምደን
ዒላማ አልባ የደነበሸ ጥይት እንተኳኮሳለን ፤
ድርቅ ሆነ ርሃብ ፤
10 ሆነ 15 ሚሊየን ፤
ሰሜን ሆነ ደቡብ ፤
ክርክራችን ለዚህ በርሃብ አንጀቱ ለታጠፈ ኢትዮጵያዊ ምን ይጠቅመወቀል እንጀራ ውይስ ውሃ ይሆነዋል?
የሰው ልጅ ክቡር እየወደቀ ነው፡፡
ሰው የሚበላ ይፈልጋል በውሃ ጥም ጉሮሮው ደርቋል…ርሀብ እሞሸለቀው ነው ፡፡

ይህ ደግና ኩሩ ህዝብ 90 ሚሊየን ቤተሰቡን በጫንቃው የተሸከመው ታታሪ ገበሬ አቅቶተታል ፡፡

የደፈረሰ እንባውን የሚያብስለት፤ርሀቡን የሚያስታግስለት ወገን ይፈልጋል ፡፡
ምዕራብያኑን ’’የስንዴያለህ  ???’’ ብለን በራቸውን ብናንኳኳ በራሰቸው የቤት ስራና ቅድሚያ በሚሰጡት ነገር ተጠምደዋልና ፤ ወደውስጣችን እንመለስ ፡፡
ምክንያቱ ምንም ይሁን ምን ወገናችን ተርበቧል ፤
ይህ ደግ ህዝብ አቅቶታል፡፡
ይህ ደግ ህዝብ እኛኝ ይሻል፡፡
አዎእኛኝይሻል …..ጎራውን እንተውውና …ለዚህ ጨዋና ኩሩ ህዝብ አሁኑኑ እንድረስለት፡፡
አሁኑኑ !!!!!
’’ዜጎቿን ለማስራብ እየተጋች ያለች ሀገር ኢትዮጵያ !’’……. ከሚል ስላቅ ለመዳን ትልቅ የቤት ስራ ይጠበቅብናል፡፡
መቼም ኢትዮጵያ ልጆቿን ለማስራብ እነደማትተጋ ይታወቃል፡፡

ተው በለው !

ተው በለው !


Published on Jan 11, 2014
New Ethiopian Music 2014 Addis Mulat - Tewbelew 

Tuesday, August 18, 2015

ዳግማዊ ዐፄ ምኒልክ ከተናገሯቸው ታሪካዊ ንግግሮች በጥቂቱ !

ዛሬ በማህበራዊ ድረገጽ  ከተቀባበልናቸው ነገሮች ታሪካዊ ቀንነቱን በመንተረራስ ዳግማዊ አጤ ምኒልክና (እምዩ ምኒልክ)
እቴጌ ጣይቱ (ብርሃን ዘ ኢትዮጵያ) የተወለዱብት ቀን ዝክርን  ነው ፡፡

እኔም ካየሁት ላካፍላችሁ



- ሰው ሁሉ እኩል ስለሆነ ማንም ሰው ሰውን ባሪያ አይበል ።
- ሁሉም ሰው በየኃይማኖቱ ይደር ።

-
ድኻ እወደደበት ቦታ ይቀመጥ በዘር በወገን ልዩነት አይከልከል

-
የመሬት ጥያቄ ላቀረቡ የውጭ አገር ሰዎች ንጉሡ የሰጡት መልስ፡- ‹‹ የኛ አገር ፍትሐ ነገሥት ልዑሎች መሬት ይሽጡ አይልም ያገሬ መሬት ባለቤቱ ሌላ ነው ከአባቶቻቸው እየተቀበሉ ያቆዩት መሬት ነው ... መሬቱ የሁሉም ስለሆነ አይሸጥም ማንም ሰው መሬቱን ሊሸጥ አይችልም መሬትን መሸጥ፣ መስጠትም የሚችለው የመሬቱ ጌታ ነው ››

-
ለመንግሥት ተሿሚዎች የሰጡት መመሪያ፡- ‹‹… እንቅልፍ ሳትወዱ መጠጥ ሳታበዙ፣ ገንዘብን ጠልታችሁ ተግታችሁ ሥራችሁን ፈጽሙ እኔ እናንተን ስለአመንኩ እናንተም የምታምኑትን ገንዘብ የማይወደውን፣ ድኻ የማይበድለውንና የሚረዳችሁን ሰው እያመለከታችሁኝ ከሥራው በመግባት መንግሥታችንን እርዱ ››

-
በጣም ወደኋላ የቀረን ሕዝቦች ነን ገና የሚሠራ ብዙ ሥራ ስላለ ወጣቶቻችን መማር አለባቸው

-
አባት ያለህ የአባትህን እሰጥሀለሁ፤ አባትህን መርቅ አባት የሌለህ አባትህ እኔ ነኝና ደጅ ጥናኝ

-
እኔ ቤት እንጀራ የለም እንጀራ ያለው ትምህርት ቤት ስለሆነ እሠራሁት ትምህርት ቤት ልጆቻችሁም እያስገባችሁ አስተምሩ

-
የኔ ርስት ኢትዮጵያ ናት የግል ርስት አልፈልግም ደግሞስ የተሾምነው እርስት ከተካፈልን ለሕዝቡ ማን ያካፍለዋል?

-
ሐገራችን አንድትለማ የሚቀርቡንን ሁሉ በታላቅ ደስታና በአክብሮት እንቀበላቸዋለን በሌላ ለሚመጡብን ግን ሁላችን ሳናልቅ ሀገራችንን ለባዕድ አሳልፈን እንሰጥም

-
የሚጠሉህን ሰዎች ከማጥፋት የሚጠላብህን ማጥፋት እንዲሉ የሸፈቱባቸውን የወጉአቸውንና ያሤሩባቸውን ሰዎች በጋብቻ በዝምድና ወይም ወዳጅ አድርገው ያቀርባሉ እንጂ ክፉን በክፉ መመለስና መበቀልን አይሹም
- አንድ የፈረንሳይ ዜጋ የቦታ ግዥ ፈቃድ ሲጠይቃቸው ምኒልክ በሰጡት መልስ - ‹‹ ያገሬ መሬት የሁሉም ኢትዮጵያዊ ስለሆነ መሬት መሸጥ መለወጥ የሚችለው ሕዝቡ ነው ደግሞስ የውጭ ዜጎች መሬት እንዲገዙ ከፈቀድኩና ባለመሬት ከሆኑ ለኔ ምን ቀርቶ እገዛለሁ ? ›› አሉ
እቴጌ ጣይቱ ብጡል ለወራሪውና ለፋሺስቱ ጣልያን ከተናገሩት ታሪካዊ ንግግር በከፊል : -
" እኔ ሴት ነኝ ፡፡ ጦርነት አልወድም ፤ ነገር ግን ሀገሬን እንደዚህ ያለ ክብር የሚነካ ዘለፋ ከምትሸከም ጦርነትን እመርጣለሁ ፡፡ ሂድ መንገዱን ጨርቅ ያድርግልህ ! እግሩን ለጠጠር ደረቱን ለጦር አስጥቶ ደሙን ለሀገሩ ፍቅር አፍስሶ ለአፈሩ ክብር ለብሶ እሱ ወድቆ ሀገሩን የማያቆም እዚህ ያለ እንዳይመስልህ ! ሂድ! የኢትዮጲያን ሰው ባታውቀው ነው፡፡ ለሀገሩ መሞት ማለት ለሀበሻ ጌጡ ነው ፡፡ ሂድ ባሻህ ግዜ ተመለስ ተሰናድተን እንጠብቅሃለን ፡፡ ያንተን ወንድነትና የጣይቱን ሴትነትም ያን ግዜ እናየዋለን ሂድ መንገዱን ጨርቅ ያድርግልህ ፡፡ "
ስለሰውነት ክብር ፣ ስለሀገር ነፃነት ለሚቆረቆሩት ለእምዬ ምኒልክ 171 ኛ እና ለእቴጌ ጣይቱ ብጡል 175 ኛ መልካም የልደታቸው መታሰቢያ ዕለት ይሁን !!!
" ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር "