Friday, July 26, 2013

ከበደ ሚካኤል እና ሙዚቃ




ሙዚቃ አየህ ልጄ የነፍስ ምግብ ነው፡፡ እኔም ለነፍሴ ሙዚቃን ማዳመጥ እወዳለሁ፡፡ ካስፈለገም ደግሞ አንጎራጉራለሁ፡፡ መቼም የራሴን ነፍስ በማንጎራጎር ማስደሰት አይሳነኝ፡፡ የክላሲካል ሙዚቃና የጥንታዊ ሙዚቃዎች ቃናና ለዛ ለኔ ጆሮ የማይጎረብጡ ቅመሞች ናቸው፡፡ ከሀገራችንም የጥንት አዝማሪዎች ግጥምም ሆነ ዜማ ይጥመኛል፡፡ የዛሬው ካለኔ ማን ተፈጥሮ ያውቃል ባይ ከሙዚቃው ማስታወቂያው ይበልጥብኛል፡፡ የግጥሙንም የዜማውንም ነገር ባላነሳው ይሻለኛል፡፡ የጥንቶቹን እነንጋቷ ከልካይን እስቲ የምታስንቅ ለዛ ያላት ዘፋኝ ጥራልኝ? ውሸት! ማንም አያህላቸው፡፡ የምወደውን አይነት ሙዚቃም አዳምጥ የነበረው ከባለቤቴ ጋር ሆኜ ከቤቴ ነው፡፡ በመኪና መንገድ ሙዚቃ እኔ አላውቅም፡፡ ይህን ያህል ካልኩህ ይበቃሃል፡፡
የካቲት መጽሔት ሐምሌ 1983 .


የተማረ ሆኖ እውነቱን የማይገልጽ
ባለ ጸጋ ሆኖ ገንዘቡን የማይሰጥ፣
ደሃ ሆኖ መስራት የማይሻ ልቡ፣
ሶስቱም ፍሬ ቢሶች፣
ለምንም አይረቡ።
……..
አይነ የለውም አሉ የሰነፍ ልመና
ወደ አምላክ ሲጸልይ ማታ በልቦና
መንገዱ ሳይመታኝ ባቧራ በጭቃ
አድርገኝ ይለዋል ላገሬ እንድበቃ
እንጦጦ ተኝቼ ሃረር እንድነቃ
………
መርዝም መድሃኒት ነው ሲሆን በጠብታ
እንዲሁም ለተንኮል አለው ቦታ ቦታ
ምን ቢሰለጥኑ ቢራቀቁ በጣም
ሁልጊዜ ደጋግሞ ብልጠት አያዋጣም።
በጅ የተበተቡት ተንኮል ዞሮ ዞሮ
ማጋለጡ አይቀር እጅና እግር አስሮ
መጽሓፉም ይለናል ሲያስተምረን ጥበብ
ብልጥ ሁን እንደባብ የዋህ ሁን እንደርግብ
ስለዚህ በብልጠት ተንኮል ስትሰሩ
በዝቶ እንዳይገላችሁ ገርነት ጨምሩ ...

የዕውቀት ብልጭታ የተወሰደ
 

No comments:

Post a Comment